በእስካሁኑ ሂደት በስኳር ፋብሪካዎቹ ወቅታዊ ቁመና ላይ ቴክኒካል ምዘና ማድረግ፣ ፋብሪካዎቹ ወደ ግል ይዞታነት በሚቀየሩበት ወቅት ሊኖር የሚገባው የስኳር ገበያ ምን መምሰል እንዳለበት የሚያሳይ ወይም የገበያ ስትራቴጅ መጠናቀቁን የገንዘብ ሚኒስቴር አማካሪ ዶክተር ብሩክ ታዬ ገልጸዋል፡፡
የስኳር ፋብሪካዎቹን ወደ ግሉ የማዛወር ሂደቱ ሁለት አመት ቢሞላውም እስካሁን ወደ ግሉ ዘርፍ የተዛወረ ፋብሪካ የለም፡፡ ዶክተር ብሩክ ጉዳዩ ጥንቃቄ የሚያስፈልገው እና በርከት ያሉ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች ወሳኝ በመሆናቸው ሂደቱን ለመፈጸም ቁርጥ ያለ ቀን ማስቀመጥ እንደሚከብድ ያስረዳሉ፡፡
የስኳር ፋብሪካዎቹን የመግዛት ወይም በጋራ የመስራት ፍላጎት ያላቸውን አካላት ለመለየት በተከናወነ የፍላጎት መጠየቂያ ጥናት እስካሁን 30 የሚደርሱ ተቋማት ዘርፉን መቀላቀል እንደሚፈልጉ መታወቁን ገልጸዋል፡፡
መተሃራ፣ ፊንጫ እና ወንጅ ስኳር ፋብሪካዎች ለጊዜው በመንግስት ስር ይቆያሉ ተብሏል፡፡ ወልቃይት፣ በለስ 1 እና 2 ፣ ቀሰም እና ሌሎች ቀሪ ፋብሪካዎች በመጀመሪያ ምዕራፍ ወደ ግል ይዞታነት ይሸጋገራሉ ተብሏል፡፡
[FBC]

