ሊቀመንበሩ በጽህፈት ቤታቸው በኩል ባወጡት መግለጫ፣ እ.ኤ.አ በ1896 የተመዘገበው የአድዋ ድል አፍሪካውያን የቅኝ ግዛትን ቀንበር ሰብረው የራሳቸውን ዕድል በራሳቸው መወሰን እንደሚችሉ ለዓለም ያሳዩበት ታሪካዊ ክስተት መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል።
"አድዋ የአፍሪካ ሉዓላዊነት፣ ክብር እና አንድነት የታየበት ታላቅ አሻራ ነው" ያሉት ሊቀመንበሩ፤ ድሉ አኅጉሪቱ ዛሬ ለምትከተለው "አጀንዳ 2063" እና "ለተባበረች አፍሪካ" ርዕይ ዋነኛ መሠረት መሆኑን አመላክተዋል።
ማህሙድ አሊ ዩሱፍ አክለውም፣ አፍሪካውያን ዛሬ የሚገጥሟቸውን ዘመናዊ ተግዳሮቶች ለማሸነፍ ያ ድል ያስገኘውን የአንድነትና የፅናት መንፈስ ሊላበሱ እንደሚገባ ጥሪ አቅርበዋል።
በተለይም ኅብረቱ የ2025ቱን ዓመት "የካሳ ክፍያ ዓመት" በማድረግ ላለፉት በደሎች ፍትህ ለመጠየቅ የሚያደርገውን ጥረት አድዋ ትልቅ ሞራል እንደሚሰጠው ጠቁመዋል።
የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን በመላው አህጉሪቱ ሰላምን ለማስፈን፣ የኢኮኖሚ ውሕደትን ለማፋጠን እና የጋራ ብልፅግናን ለማረጋገጥ ቁርጠኛ ነው ብለዋል።

