ሁለቱን ተርባይኖች ኃይል ማመንጨት የሚያስችለው ሁለተኛው ዙር የህዳሴ ግድብ ውኃ መሙላቱን መንግስት አበሰረ
በርካቶች በጉጉት ሲጠብቁት የነበረውን የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ሙሌት ተገባዶ ውሃው በግድቡ አናት ላይ መፍሰሱን የኢትዮጵያ የውሃ፣ መስኖ እና ኢነርጂ ሚኒስትር ዶክተር ኢንጂነር ስለሺ በቀለ ከጉባ አስታውቀዋል፡፡
ሚኒስትሩ በትዊተር ገፃቸው ባሰፈሩት የደስታ መግለጫ “ዛሬ ሀምሌ 12 ቀን 2013 ዓ/ም የሁለተኛውን አመት የህዳሴ ግድብ ሙሌት ተገባዶ ውሃው በግድቡ አናት ላይ ፈሶአል። ኢትዮጵያውያን እና የኢትዮጵያ ወዳጆችም እንኩዋን ደስ አላችሁ” ብለዋል።
ሚኒስትሩ አክለውም “ይህ ውጤት ማለት 2 ተርባይኖችን ለማንቀሳቀስ የሚያስፈልገውን የውሃ መጠንና ይዘናል ማለት ነው ፣ ይህም ከፈጣሪ የተሰጠን ፀጋ ምን ያህል ትልቅ እንደሆነና እንዴት እያገዘን እንደሆነ መረዳት እንችላለን። ለዚሁም ምስጋና ይግባው። እዚህ ደረጃ ለመድረስ በዘንድሮው ዓመት መጠነ ሰፊ ስራ ሰርተናል። በቀጣይ ሁለቱ ተርባይኖች ኃይል እንዲያመነጩ ብርቱ ስራዎች እየተሰሩ ነው፤ እናም ያንን በቅርብ ወራት በማጠናቀቅ ልፋታችንን ውጤት ላይ እናደርሳለን” ብለዋል፡፡
[ ደመቀ ከበደ ፡ አዲስ አበባ ]

