በታላቁ ሕዳሴ ግድብ ዙሪያ ኢትዮጵያ፣ ግብፅና ሱዳንን አካትቶ በተባበሩት መንግሥታት ፀጥታ ምክር ቤት ሐሙስ ጁላይ 8 የተካሔደው ስብሰባ ያለ ስምምነት ተጠናቅቋል።
ስብሰባው የተጠራው በግብፅና ሱዳን ስም በቱኒዝያ አማካይነት የነበረ ሲሆን፤ ለንግግር የቀረበውም "ሰላምና ፀጥታ ለአፍሪካ" በሚል አጀንዳ ስር ነው።
በዕለቱም የተመድ ዋና ፀሐፊ የአፍሪካ ቀንድ ልዩ ልዑክ ፓርፌይት ኦናንጋ አንያንጋና የወቅቱ የአፍሪካ ኅብረትና በተመድ የዲሞክራቲክ ኮንጎ ሪፐብሊክ ተወካይ፣ ወ/ሮ ኢንገር አንደርሰን የተመድ የተፈጥሮ ጥበቃ ኃላፊ፣ የኢትዮጵያ የውኃና መስኖ ልማት ሚኒስትር ኢንጂነር ዶ/ር ስለሺ በቀለ፣ የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳሜህ ሐሰን ሹክሪና የሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሜሪየም አል ሳዲቅ አል ማህዲ በዋነኛ ተናጋሪነት አተያያቸውንና የየአገራቱን አቋምና ፍላጎቶችን ለምክር ቤቱ አስደምጠዋል።
የሕዳሴ ግድብ ጉዳይ የፀጥታ ምክር ቤት ፊት ሲቀርብ የጁላይ 8ቱ ለሁለተኛ ጊዜ ሲሆን ቀደም ሲልም ጁን 29, 2020 ቀርቧል።
የሐሙስ ጁላይ 8 ስብሰባ ጠሪ የሆነችው ቱኒዝያ ጁላይ 2 ለፀጥታ ምክር ቤት አባላቱ ባሰራጨችው ረቂቅ፤
- ኢትዮጵያ፣ ግብፅና ሱዳን ሕጋዊ አስገዳጅነት ወዳለው ስምምነት ላይ በስድስት ወራት ለመድረስ በድርድር ሂደቱ እንዲቀጥሉ
- በተናጠል የግድቡን ሙሌት ማካሔድ አግባብ እንዳልሆነ
- በአፍሪካ ኅብረት በሚመራው የሶስቱ አገራት ድርድር ሂደት ላይ በታዛቢነት የሚገኙት ዩናይትድ ስቴትስና የአውሮፓ ኅብረት ይበልጥ ሚና እንዲኖራቸው
- የፀጥታ ምክር ቤቱ ጉዳዩን በዘላቂነት እንዲመለከተው የሚያበረታታ ነው።

ይሁንና የቱኒዝያ የውኃ ልማትና አስተዳደር ጉዳይ በፀጥታው ምክር ቤት በዘላቂነት እንዲታይ የመሻት ዕሳቤ በበርካታ አገራት ዘንድ አሉታዊ አተያዮችን አሳድሯል።
ሐሙስ ዕለት በተካሔደው የምክር ቤቱ ስብሰባ ላይ በወቅቱ የአፍሪካ ኅብረትና በተመድ የዲሞክራቲክ ኮንጎ ሪፐብሊክ ተወካይነት ንግግራቸውን ያስደመጡት ኢንገር አንደርሰን "90 ፐርሰንት ያህል ቴክኒካዊ ችግሮች ተፈትተዋል፤ ቀሪው ለፊርማ የሚያበቃ በድርቅ ወቅት የውኃ ፍሰት አያያዝ ላይ ዕልባት የሚሹ ቴክኒካዊና ሕጋዊ ልዩነቶችን መፍታት ነው" ብለዋል።

ወ/ሮ ኢንገር አንደርሰን የተመድ የተፈጥሮ ጥበቃ ኃላፊም በበኩላቸው ሶስቱ አገራት የግድ ከስምምነት ላይ መድረስ እንደሚገባቸው አስገንዝበው፤ ከስምምነት ላይ እንዲደርሱም ተመድ ሶስቱን ተደራዳሪ አገራትና የአፍሪካ ኅብረትን ለመርዳት ዝግጁ መሆኑን ገልጠዋል።
በተመድ የእንግሊዝ ተወካይዋ ባርባራ ዉድዋርድ በበኩላቸው ሶስቱ አገራት የተናጠል እርምጃ ከመውሰድ እንዲቆጠቡ በማሳሳብ በአፍሪካ ኅብረት አደራዳሪነት ገንቢ የሆነ ድርድር እንዲያካሄዱ አበረታተዋል። እንግሊዝ ከሶስቱም አገራት ጋር የቅርብ ኝኙነት ያላት መሆኑንም ተናግረዋል።
በተመድ የዩናይትድ ስቴትስ አምባሳደር ሊንዳ ቶማስ - ግሪንፊልድ በፊናቸው አገራቸው የታላቁ ሕዳሴ ግድብን ጉዳይ "ሚዛናዊና ፍትሐዊ" በሆነ መልኩ ለመፍታት እንዲቻል ድጋፍና ትብብር ለማድረግ ዝግጁ መሆኗን አስታውቀዋል። አክለውም የሕዳሴ ግድብን ጉዳይ ለመፍታት የአፍሪካ ኅብረት ተገቢው መድረክ መሆኑን በመጥቀስ "ሶስቱም አገራት ድርድሮቹን ሊያደናቅፍ ከሚችሉ የተናጠል ድርጊት ወይም መግለጫ እንዲቆጠቡ እናበረታታለን" ብለዋል።

በተመድ ቋሚ የሩስያ አምባሳደር ቫሲሊ ኔቤንዝያ በበኩላቸው የሩሲያ ፌዴሬሽን የታላቁን ሕዳሴ ግድብ በቅርበት የሚከታተል መሆኑን ጠቁመው በሶስቱ አገራት መካክል ያሉ ልዩነቶች በአፍሪካ ሕብረት አማካይነት እንዲፈታ አመላክተዋል። ኢትዮጵያ፣ ግብፅና ሱዳን የሚስማሙ ከሆነ ሩስያ የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ሙሌት ሂደትን በሳተላይት ክትትል ማድረግ እንደምትችል ገልጠዋል።
ቻይናና ሕንድም በበኩላቸው በሶስቱ አገራት መካከል ያሉት ልዩነቶች በአፍሪካ ኅብረት በኩል እንዲፈታ አሳስበዋል።
የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳሜህ ሐሰን ሹክሪ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በ100 ሚሊየን የግብፅ ሕዝብ ላይ አደጋ እንደሚሆን፤ በተለይም በድርቅ ወቅት በእጅጉ አሳሳቢ መሆኑን ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ የተመድ ፀጥታ ምክር ቤት ተሰይሞ ከመምከሩና ሕጋዊ አስገዳጅነት ካለው ስምምነት ሳይደረስ የሁለተኛ ዙር ሙሌት መጀመሯን በማንሳት ተቃውሟቸውን አሰምተዋል። አዲስ አበባ ለዓለም አቀፍ ሕግ ተገዢ አይደለችም ሲሉም ከስሰዋል።
የተመድ ፀጥታ ምክር ቤት 15ቱ አባል አገራትም የሰላምና ፀጥታ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ሲሉ ጥሪ አቅርበዋል።

የሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሜሪየም አል ሳዲቅ አል ማህዲ የፀጥታው ምክር ቤት የሕዳሴ ግድብን ችግሮች ለመፍታት አዎንታዊ ሚና እንዲጫወት ጥሪ ያቀረቡ ሲሆን፤ ሱዳን በአፍሪካ ሕበረት አደራዳሪነት በውኃ ሙሌትና የግድቡ አካሄድ ላይ ሕጋዊ አስገዳጅ ማሰሪያ ካለው ስምምነት የመድረስን አስፈላጊነት በብርቱ እንደምትቀጥልበት አመላክተዋል።

ሕጋዊ አስገዳጅ ማሰሪያ ካለው ስምምነትም ለሱዳንና ግብፅ ሕዝቦች አደጋ ሊሆን እንደሚችል ተናግረዋል።
ሆኖም አገራቸው በታችኛው ተፋሳሽ አገራት ላይ ጉዳት የማያደርስን የኢትዮጵያ የልማት መብት እንደምትደግፍ ገልጠዋል።
የሕዳሴ ግድብን አስመልክቶ የሱዳን ሶስት ዋነኛ ጉዳይ ያሏቸውንም ሲጠቅሱም " የሱዳን ዜጎች ደኅንነት፣ የሱዳን ግድቦች ደኅንነትና የሱዳን ስትራቴጂያዊ ደኅነነት" እንደሆኑ አስታውቀዋል።
ለተመድ ፀጥታ ምክር ቤት አባል አገራት፣ ለግብፅና ሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትራት የኢትዮጵያን አቋም ያስታውቁት የውኃና መስኖ ልማት ሚኒስትር ኢንጂነር ዶ/ር ስለሺ በቀለ በበኩላቸው ኢትዮጵያ ከጎረቤት አገራቱ ጋር ትብብር እንደምታደርግ ገልጠው ሆኖም ኢትዮጵያ ለፖለቲካዊ ጫና እንደማትገበር አስታውቀዋል።
ግብፅና ሱዳን በቅኝ ዘመን አብላጫ ተጠቃሚነት መቀጠል እንደሚሹ ጠቁመው፤ ግብፅና ሱዳን ጉዳዩን ለተመድ ፀጥታ ምክር ቤት ማቅረባቸው አሳዛኝ መሆኑን በማንሳት ነቅፈዋል።

በ5 ቢሊየን ዶላርስ ወጪ እየተገነባ ያለው ግድብ ሙሉ በሙሉ ለመጠናቀቅ መቃረቡንም አስታውቀዋል።
ሲሉም አስገንዝበዋል።

