የተባበሩት መንግሥታት የጸጥታ ምክር ቤት ኢትዮጵያ፣ ግብፅና ሱዳንን በታላቁ ሕዳሴ ግድብ ዙሪያ ለማሸማገል ከመከረ በኋላ ጉዳዩ በአፍሪካ ሕብረት እንዲታይ ማሳሰቡ ይታወሳል። ይህንኑ የመግሥታቱ አገራት ድርጅት ምክረ ሃሳብ ተከትሎም ለ11 ቀናት በውኃ ሚኒስትሮች አማካይነት የተካሄደው የሶስትዮሽ ድርድር ከስምምነት ላይ ሳይደርስ አክትሟል።
የድረድሩን ሂደትና ክሽፈት አስመልክቶ በኢትዮጵያ በኩል ለአፍሪካ ሕብረትና መሪዎች ቢሮ ሪፖርት ተሰናድቶ እንደሚላክና የመሪዎችን መመሪያዎች ተከትሎም ቀጣይ ውይይቶች እንደሚኖሩ የውኃና መስኖ ሚኒስቴር ሚኒስትር ኢንጂነር ስለሺ በቀለ በቲዊተር ገጻቸው አስታውቀዋል።

የግብፅ የውኃና መስኖ ሚኒስቴርም በበኩሉ ባወጣው መግለጫ፤
"ለ11 ቀናት በአፍሪካ ሕብረት አማካይነት የታላቁን ሕዳሴ ግድብ ሙሌትና የግድቡን ሥራ ክንውን አስመልክቶ የሶስቱ አገራት የውኃ ሚኒስትሮች፣ የአገራት ተወካዮችና ታዛቢዎች በተገኘኙበት የተካሔደው ድርድር ጁላይ 13 ተጠናቅቋል "
"የሚኒስትሮቹን ስብሰባ ተከትሎ የሶስቱ አገራት ቴክኒክና የሕግ ኮሚቴዎች ክለሳ ዋነኛ በሆኑት የሕዳሴ ግድብ ሙሌትና የግድቡ ሥራ ክንዋኔ ላይ ልዩነቶች ዕልባት ሳያገኙ መቀጠላቸው ተንጸባርቋል"
"በስብሰባው ማብቂያ ላይም ሚኒስትሮቹ እያንዳንዱ አገር ለቀጣዩ ድርድር መሸጋገሪያ ሆኖ መለስተኛ የአፍሪካ ጉባኤን ለማካሔድ የመጨረሻ ሪፖርቱን ለወቅቱ የአፍሪካ ሕብረት ፕሬዚደንት ወደ ደቡብ አፍሪካ ለመላክ ተስማምተዋል" ሲል አስታውቋል።
የድርድሩን ሂደት አስመክልቶ ሱዳን ወደ ደቡብ አፍሪካ ለወቅቱ የአፍሪካ ሕብረት ፕሬዚደንት በላከችው ሪፖርቷ በድረድሩ ወቅት "ሁነኛ በሆኑ ጉዳዮች" ላይ "መጠነኛ መሻሻል" መታያታቸውን አስፍራለች።
ሱዳን ከሪፖርቷ ጋር "በሶስቱ አገራት ተቀባይነት የሚኖረው ሚዛናዊና ፍትሓዊ" ረቂቅ ስምምነት አያይዛ መላኳን አስታውቃለች።
በቀጣይነትም የሶስቱን አገራት ሪፖርትና አማራጭ የስምምነት መፍትሔ ምክረ ሃሳቦች ከተቀበሉ በኋላ የወቅቱ የአፍሪካ ሕብረት ፕሬዚደንት የሆኑት የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚደንት መለስተኛ የአፍሪካ ሕብረት ጉባኤን ከመጥራታቸው በፊት የሶስቱን አገራት መሪዎችና የአፍሪካ ቢሮ ኃላፊዎችን ደውለው እንደሚያነጋግሩ ይጠበቃል።

