የዩናይትድ ስቴትስ ግምጃ ቤት መምሪያ ትናንት ሰኞ ኦገስት 23 በኤርትራ የጦር ኃይሎች ልዩ ረዳት ጄኔራል ፊሊፖስ ወልደዮሃንስ ላይ ትግራይ ውስጥ በተፈጸመ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት እጃቸው አለበት በሚል ሳቢያ እገዳ ጥሏል።
መምሪያው እንዳስታወቀው በጦር ኃይሎች ልዩ ረዳቱ ላይ እገዳው የተጣለው የጅምላ ጭፍጨፋ፣ መጠነ ሰፊ ወሲባዊ ጥቃትና ሆን ተብሎ በሰላማዊ ሰዎች ላይ የጎዳና ግድያ ፍጸማዎችን ያካተተውን ሉላዊ ማግኒትስኪ የሰብዓዊ መብቶች የተጠያቂነት አንቀጽ ተከትሎ እንደሆነ አስታውቋል።
የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከንም በበኩላቸው "ዩናይትድ ስቴትስ ኢትዮጵያ ውስጥ በብርቱ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች፣ ለግጭቱ መራዘምና የሰብዓዊ ቀውስ ክስተት ላይ የተሳትፉትን በመለየትና እርምጃ መውሰዱን ትቀጥልበታለች" ብለዋል።
የእገዳ እርምጃውን አስመልክቶ የኤርትራ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በሰጠው ምላሽ የዋሽንግተን እርምጃ "ፍፁም መሠረተ ቢስ የሆነ ውንጀላ ነው፤ የዩናይትድ ስቴትስ አስተዳደር በእርግጥም ለሐሰት ክሶቹ ማስረጃ አለኝ የሚል ከሆነ ጉዳዩን ለገለልተኛ ዳኝነት እንዲያቀርብ ኤርትራ ጥሪ ታቀርባለች" ብሏል።

