የኢትዮጵያ መንግስት ሁሉም የፌዴራል እና የክልል ሲቪልና ወታደራዊ ተቋማት፣ ከመንግሥት በሚሰጣቸው ዝርዝር አፈጻጸም መሠረት በትግራይ ክልል የተኩስ አቁም እንዲያከብሩ እና እንዲያስከብሩ መታዘዛቸውን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ምሽቱን ባወጣው መግለጫ “ይሄን መልካም ዕድል ለክፉ የሚጠቀሙ ወገኖች ካጋጠሙ ግን አስፈላጊው ሕግን የማስከበር ተግባር እንደ አግባቡ የሚከናወን ይሆናል” ሲል አስጠንቅቋል።
የተኩስ አቁሙን እርምጃ አስመልክቶ የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ የድርጅታቸውን 350,000 ያህል ሰዎች በትግራይ ለረሃብ መዳረግ ጫፍ ላይ ናቸው ማለትን ተከትሎ ትግራይ ውስጥ ውጤታማ የሆነ ተኩስ አቁም እንዲደረግ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ጋር መነጋገራቸውን በቲዊተር ገፃቸው አስታውቀዋል።

ከጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት መግለጫ ቀደም ብሎ ኢዜአ እንደዘገበው የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር የፌዴራል መንግስት ሰብዓዊነትን መሰረት ባደረገና ተጨማሪ ጉዳት በማያስከትል መልኩ የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲያደርግ ጥያቄ አቅርቧል።
የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶክተር አብርሃም በላይ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንዳስታወቁት "ክረምት እየገባ በመሆኑ የትግራይ አርሶ አደር ተረጋግቶ የእርሻ ስራውን እንዲያከናውን፣ የሰብዓዊ ድጋፍ ለተረጂዎች ያለምንም ችግር እንዲደርስ ወቅቱን የሚመጥን ፖለቲካዊ መፍትሄ ለመስጠት የፌዴራል መንግስት የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲያደርግ" መጠየቁን ገልጠዋል።
ጊዜያዊ አስተዳደሩ ከእዚህ ውሳኔ ላይ የደረሰውም "የክልሉን ወቅታዊ ሁኔታ አስመልክቶ ከክልሉ ህዝብ ተወካዮች፣ ከቢሮና ዞኖች አመራር አባላት፣ በተለያየ ቦታ ከሚገኙ የትግራይ ተወላጆች፣ ከትግራይ ምሁራን፣ ከባለሀብቶችና ከሃይማኖት አባቶች ጋር ተከታታይ ምክክር ካደረገ በኋላ ነው " ብለዋል።
አክለውም "ዘጠኝ ነጥቦች ያካተተ ጥያቄ ለፌዴራል መንግሥት አቅርቧል፤ በቀጣይም ፖለቲካ አማራጮችን ታሳቢ ማደረግና መፍትሄ እርምጃዎች የመውሰድ አስፈላጊነት ላይ እምነት መኖሩንና በአሁኑ ወቅት በረሃ ካለው ሃይል መካከል የሰላም መንገድ የሚፈልግ እንዳለ" ለኢዜአ ተናግረዋል።
በሌላ በኩል የሚወጡ ሪፖርቶች እንደሚያመለክቱት ከሆነ ይትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደርና የመከላከያ ሠራዊቱ መቀሌን ለቅቀው መውጣታቸውን ጠቁመዋል። የሕወሓት ቃል አቀባይ ገታችሀው ረዳ መቀሌ በታጣቂዎች ቁጥጥር ስር መሆኗን ለሮይተርስ ገልጠዋል።
ሌሎች ዓለም አቀፍ የብዙኅን መገናኛ አውታሮች በኩልም በመቀሌ መንገዶች ላይ የደስታ ተኩሶች መሰማታቸውን ዘግበዋል።
ሆኖም እስካሁን በኢትዮጵያ መንግሥት በኩል የመቀሌን በታጣቂዎች እጅ መውደቅና የሠራዊቱንም ከከተማይቱ መልቀቅ አስመልክቶ ማስተባበያም ሆነ ማረጋገጫ አልሰጠበትም።
በሕወሓት በኩልም የተኩስ አቁሙን አስመልክቶ ለጊዜው ይፋዊ መግለጫ አልተሰጠም።

