የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ነሐሴ 20 ቀን 2013 ዓ.ም. ባወጣው ጋዜጣዊ መግለጫ በኦሮሚያ ክልል፣ ምስራቅ ወለጋ ዞን፣ ጊዳ ኪራሙ ወረዳ ነሐሴ 11 ቀን 2013 ዓ.ም. በአካባቢው ተሰማርተው የነበሩ የፀጥታ ኃይሎች ወደ ሌላ አካባቢ መንቀሳቀሳቸውን ተከትሎ፣ ነሃሴ 12 ቀን 2013 ዓ.ም. የ”ኦነግ ሸኔ” ናቸው በተባሉ ታጣቂዎች በአካባቢው ነዋሪዎች ላይ ብሔርን መሰረት ያደረገ ጥቃት ማድረሳቸው በከፍተኛ ሁኔታ አሳሳቢ መሆኑን ገለጸ።
አያይዞም፤ ነሐሴ 12 ቀን 2013 ዓ.ም. በታጣቂዎች በተፈጸመው ጥቃት ከ150 በላይ ነዋሪዎች መገደላቸውን የአካባቢው ነዋሪዎችና ሌሎች ሰዎች ለኮሚሽኑ ማስረዳታቸውን አስታውቋል።
በሌላም በኩል የወረዳው ነዋሪዎች፣ በተለይም ሴቶችና ሕጻናት ወደ አጎራባች አካባቢዎች መሸሻቸውንና በቀጣይ ቀናት ከነዋሪዎች የተውጣጡ ሰዎች ብሔርን መሰረት ያደረገ የአጸፋ ጥቃት በማድረሳቸው 60 ሰዎች መገደላቸውን፣ ነዋሪዎችም ወደ አማራ ክልልና ወደ ኪራሙ ከተማ መፈናቀላቸውን ኮሚሽኑ መረዳቱን አመላክቶ፤ የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ በቀዳሚነት የክልሉ የፀጥታ ኃይሎች ከፌዴራል የፀጥታ ኃይሎች ጋር እንዲቀናጁና የአካባቢውን ነዋሪዎች ደኅንነት እንዲያረጋግጡ እንዲሁም የፌዴራልና የኦሮሚያ ክልል መንግስት ለጥቃቱ መፈፀም ክፍተት የፈጠረው የፀጥታ ሀይሎች ከአከባቢው መውጣት ምክንያቱን እንዲያጣሩ በአጽንዖት ጥሪ ማቅረባቸውን አስታውቋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለም የተባበሩት መንግሥታት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬስ ለተመድ ጸጥታ ምክር ቤት ሐሙስ ዕለት እንደገለጡት ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው ግጭት ከትግራይ ክፍለ አገር አልፎ መዛመቱ ያሳሰባቸው መሆኑን ገልጠዋል።

አክለውም "ቆስቋሽ አባባሎችና የጎሳ ለይቶ ምዝገባ የአገሪቱን ማኅበራዊ ድርና ማግ እያሳሳ ነው" በማለት ለ15ቱ የምክር ቤት አባላት አሳስበዋል።
አያይዘውም፤ ሁሉም ቡድናት ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ በአስቸኳይ ግጭትን ለመግታትና ዘላቂ የሆነ ተኩስ ማቋምን በድርድር ለማስፈን እንዲችሉ ጥሪ አቅርበዋል።

