ቪክቶሪያ ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ 484 አዲስ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎችን ስታመዘግብ፤ ሁለት ሰዎችም ሕይወታቸውን አጥተዋል።
ሁለቱ ሕይወታቸው ያለፈ ሰዎች በአረጋዊያን መጦሪያ የነበሩና በ90ዎቹ ዕድሜ ያሉ ናቸው።
ይህም ቪክቶሪያ ውስጥ በቫይረሱ ሕይወታቸው ያለፈውን ሰዎች ቁጥር 44 አድርሶታል።
ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ የተከሰተው 484 የቫይረሱ ተጠቂዎች ቁጥር በአውስትራሊያ ውስጥ የመጀመሪያው ከፍተኛ መጠን ነው።
ቀደም ሲል በአገር አቀፍ ደረጃ ማርች 28 በአንድ ቀን አዲስ ተመዝግቦ የነበረው የቫይረሱ ከፍተኛ መጠን 469 ነበር።
ፕሪሚየር ዳንኤል አንድሩስ በቫይረሱ ከተያዙት ውስጥ 53 ፐርሰንቱ ራሳቸውን አግልለው ባለመቆየታቸው ቅር መሰኘታቸውን ሲገልጡ፤
"ከጁላይ 7 እስከ ጁላይ 21 ባሉት ጊዜያት 3810 በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ራሳቸውን አልገለሉም። ከ3400 በቫይረሱ ከተያዙቱ ምርመራ እስካደረጉ ድረስ ባሉት ጊዜያት ውስጥ ከአሥር ዘጠኙ ራሳቸውን አለማግለላቸውን ሪፖርት ሳደርግ በጣም፣ በጣም ደስተኛ አይደለሁም። በጣም አዝኛለሁ"
"ምርመራዎችን እስከሚያካሂዱ ድረስ ቤት ውስጥ ካልተቆየ በስተቀር ቁጥሮቹ ወደ ታች አይወርዱም። ከቶውንም እያሻቀቡ ይሄዳሉ እንጂ። የስድስት ሳምንታቱ ገደብም ለስድስት ሳምንታት ብቻ አይሆንም። ከዚያ በላይ ሊቀጥል ይችላል" ብለዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለም፤ ኒው ሳውዝ ዌይልስ ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ 16 በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎችን አስመዝግባለች።
በቫይረሱ ከተጠቁት ውስጥ አንዱ ሆቴል ውስጥ ወሸባ ገብተው ካሉት ሲሆን፤ የተቀሩት 15ቱ በማኅበረሰብ ተጋቦት የተያዙ ናቸው።

