ከጥቅምት 9 እስከ ኅዳር 9 ቀን 2013 ዓ.ም የሚቆየው የእምቦጭ አረም የማስወገድ ዘመቻ ዛሬ በይፋ ተጀምሯል።
በዘመቻው ጣና ሐይቅን የወረረውን የእምቦጭ አረም በዘላቂነት ለማስወገድ ጉልህ ሚና እንደሚኖረው ይጠበቃል።
የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ተመስገን ጥሩነህ በዘመቻው ማስጀመሪያ ላይ እንደተናገሩት "ሁሉም ኢትዮጵያዊ ዜጋ በዚህ የእምቦጭ አረም ማስወገድ ንቅናቄ ተሳታፊ እንዲሆን " በክልሉ መንግስት ስም ጥሪ አቅርበዋል፡፡
ከ2004 ዓም ጀምሮ ጣና ላይ የተከሰተው የእምቦጭ አረም በአሁኑ ወቅት በሐይቁ ዙሪያ በሚገኙ 30 ቀበሌዎች 4ሺህ 302 ሄክታር የውሃ አካሉና ዳርቻው ተወርሯል።
SBS ባገኘው መረጃ መሰረት ዛሬ ይፋ በተደረገው ዘመቻ በእያንዳንዱ ቀበሌ በቀን ከ250 እስከ 300 ሰው የሚሳተፍ ሲሆን በአጠቃላይ 360 ሺህ ህዝብ ይሳተፋል ተብሎ ይጠበቃል።
በዘመቻውም የአካባቢው ማህበረሰብና ከሌሎች አካባቢዎች የሚመጡ ግለሰቦች፣ የተቋማት ሰራተኞች፣ በጎ ፈቃደኞች፣ የጉልበት ሰራተኞችና ሌሎችም ይሳተፋሉ።
በዚህ የንቅናቄ ስራም እስከ 90 በመቶ አረሙን ለማስወገድ የታቀደ ሲሆን ለንቅናቄው ያስፈልጋል ተብሎ የሚጠበቀው ከ92 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪም ከፌደራልና ከክልሉ መንግስት እንደሚሸፈን ታውቋል።

