በታህሳሱ ግርግር ወቅት በአብዮት ቀስቃሽነትና መሪነት ለክስ የተዳረጉትን በዳኝነት ተሰይመው እንዲፈርዱ በልዑል ዓሥራተ ካሣ ይመረጣሉ። እሳቸው ራሳቸው ከለውጥ ፈላጊዎቹ አንዱ ነበሩና በአለቆቻቸው ፊት ሞገስን ለመላበስ ሲሉ ከታሪክና ከኅሊናቸው ጋር መጋጨትን አልወደዱም።
ይልቁንም ምርጫ አድርገው የዘየዱት ከአዲስ አበባ መሰወርን ነበር።
“የታሪክ አውራ የሆኑና የማከብራቸው [እነ ጄኔራል መንግሥቱ ንዋይን] ሰዎች ላይ ዳኛ ሆኜ ልፈርድባቸው ስላልፈቀድኩ ከአዲስ አበባ ጠፍቼ ወደ ሐረር ሔጄ ተደበቅኩ” ይላሉ።

ሌላኛው የሕይወት ጉዟቸው ውስጥ የገጠማቸው የታሪክ ምዕራፍ የየካቲት ‘66ቱ ሕዝባዊ አብዮት ክስተት ነው።
የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የዘውድ ሥርዓት በአዲሱ የልጅ እንዳልካቸው መኮንን መንግሥት እጅ ሲገባ ባሕር ተሻግረው ይገኙ የነበረው አገረ አሜሪካ ነበር።
አዲሱ መራሄ መንግሥት ልጅ እንዳልካቸው መኮንን ራሳቸው ለዶ/ር በረከት ስልክ መትተው እገዛቸውን እንደሚሹ ጠይቀዋቸዋል። ሆኖም የዶ/ር በረከት ምላሽ በልጃቸው የሕክምና እርዳታ መሻት ሳቢያ ‘አይቻለኝም’ የሚል ሆነ።
ይሁንና የልጅ እንዳልካቸው መንግሥት ሲያከትም፤ ወዳጃቸውና ዘመዳቸው ሌተና ጄኔራል አማን አንዶም የተተኪው የጊዜያዊው ወታደራዊ አስተዳደር ደርግ ሊቀመንበር በመሆናቸው ዳግም ወደ አገር ቤት ተጠሩ።

የዘውድ ሥርዓቱን ባለ ሥልጣናት እንዲመረምሩም በደርግ የተቋቋመው መርማሪ ኮሚሽን ምክትል ሊቀመንበር ሆነው ተሾሙ።
የዛሬው መነሻችን ከታህሳሱ የለውጥ እንቅስቃሴ ክሽፈት በኋላ የዳኝነት ስየማ ሂደት ላይ ነው።





