ፕሮፌሰር በረከት በትናንቱ የኤርትራ ሕዝብ ነፃ አውጪ ድርጅት መሪና ዛሬም ድረስ ለ፳፮ ዓመታት ኤርትራን በፕሬዚደንት እየመሩ ያሉትን ኢሳይያስ አፈወርቂን ማንነት በውል ለመረዳት እንደምን እንዳዳገታቸው ያነሳሉ።

“የኢሳይያስ አፈወርቅ ነገር ዕንቆቅልሽ ነው” ይላሉ።
ከኢሕዲሪ መንግሥት ውድቀት በኋላ ኤርትራ ለሉዓላዊት አገርነት በመብቃትዋ እንደ አገር ለመቆም ከሚያሿት ዋነኛ የመተዳደሪያ ሰነዶች መካከል ሕገ መንግሥት ነበርና የሕገ መንግሥት አርቃቂ ኮሚሽን አቆመች።
ፕሮፌሰር በረከትም የኢትዮጵያ የመጀመሪያው ጠቅላይ ዓቃቤነት የሥራ ተሞክሯቸውና ሲልም በዓለም አቀፍ ደረጃ በኢራቅ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ናይጄሪያና አፍጋኒስታን ያበረከቱት የሕገ መንግሥት ረቀቃ አስተዋጽዖዋቸው ሚዛን ደፍቶ በፕሬዚደንት ኢሳይያስ አፈወርቅ የኮሚሽኑ ሊቀመንበር ሆነው ተሰየሙ።

ከዓመታት ድካም በኋላ የሥራ ፍሬያቸውን ለአገሪቱ ፓርላማና ፕሬዚደንት አቀረቡ። ሆኖም ኤርትራ በሕገ መንግሥት ስትተዳደር የማየት ምኞታቸው ከቀን ሕልምነት አላለፈም። ኤርትራ ዛሬም ድረስ ሕገ መንግሥት የላትም።

የሕዝባቸው ርዕይ ዕውን ባለመሆኑ “እኔንም ጨምሮ፤ ከነፃ አውጪነት ዘመን ጀምሮ እስከ አሁኑ የኤርትራ መንግሥት ድረስ ላለው ታሪካዊ ሁነት ሁላችንም ተጠያቂዎች ነን” ከሚል ድምዳሜ ላይ ደርሰዋል።





