የሕዝባዊ ወያኔ ሓትነት ትግራይ (ሕወሓት) ሴፕቴምበር 11 / መስከረም አንድ ቀን ባወጣው መግለጫ ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር ተከስቶ ያለውን ግጭት በሰላማዊ መንገድ ዕልባት ለማበጀት እንደሚሻ አስታውቋል።
ሕወሓት በመግለጫው ኢትዮጵያውያን በተለይም የትግራይ ሕዝብ የተኩስ ድምፅ እንዳይሰሙ፣ ከመሠረታዊ አገልግሎቶችና ሰብዓዊ ረድኤቶች ጋር ተያያዥ ከሆኑ ስቃይና ጉስቁልናዎች ታድገው ማየት እንደሚሻ ገልጧል።
ይህንንም ዕውን ለማድረግ የትግራይ ክልላዊ መንግሥት በአፍሪካ ኅብረት መሪነት በሚካሔድ የሰላም ሂደት ለመሳተፍ ዝግጁ መሆኑ አመልክቷል።
በታካይነትም ሂደቱን ግብር ላይ ለማዋል እንዲያስችል በአስቸኳይና የጋራ ስምምነት ላይ የተደረሰበት ተኩስ አቁም ለማድረግ ስንዱ መሆኑንም አስታውቋል።
የሰላም ሂደቱም የጋራ ተቀባይነትን ያገኙ አደራዳሪዎች፣ ተደራዳሪ ወገኖች የጋራ አመኔታን እንዲገነቡ የሚያስችሉ ዓለም አቀፍ ታዛቢዎችና ለሰላም ሂደቱ አስፈላጊውን መምሪያና ምክር የሚቸሩ ጠበብትን ያቀፈ እንዲሆንም አሳቧል።
በትግራይ በኩል የተደራዳሪ ቡድን የሰየመ መሆኑንና ጄኔራል ፃድቃን ገብረትንሣኤና አቶ ጌታቸው ረዳ የተደራዳሪ ቡድን አባልነት ውክልና የተሰጣቸው መሆኑን አስታውቋል።
መግለጫው በማጠቃለው "በአዲስ ዓመት መንፈስ ፍልሚያን እናብቃ፣ ለሰላም ዕድል እንስጥ፣ ወደ ሰላምና ብልፅግና መንገድ እናምራ" ብሏል።
የአፍሪካ ኅብረትም በበኩሉ፤ ይህንኑ የትግራይ ክልል አስተዳደርን የሰላምና ድርድር ጥሪ በመልካም ጎኑ መቀበሉን ገልጦ፤ ለሂደቱ ጅማሮና ስምረትም የበኩሉን ሚና እንደሚወጣ አስታውቋል።
በሌላም በኩል የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን አገራቸው ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር እንደምትቆምና በአፍሪካ ኅብረት በመመራት እየተካሔዱ ላሉት ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች ድጋፎቿን እየቸረች ስለመሆኗ አመላክተዋል።
አክለውም፤ በኢትዮጵያ አዲስ ዓመት መንፈስ የአገሪቱ መሪዎች ኢትዮጵያን ዘላቂ ስላም ወደሚሰፍንበት መንገድ እንዲመሩ ጥሪያቸውን እንደሚያስተላልፉም ገልጠዋል።