የካቲት 16/2015 አንጋፋው እና ታዋቂው ብስክሌተኛ ገረመው ደምቦባ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል።
የብስክሌት ስፖርተኛው ገረመው ደንቦባ በሕክምና ሲረዳ ቆይቶ በትናንትናው ዕለት በ90 ዓመቱ ሕይወቱ ማለፉን ኢዜአ ከቤተሰቡ ያገኘው መረጃ ያመለክታል።
ኢትዮጵያ በተሳተፈችበት ሜልበርን ኦሎምፒክ በብስክሌት ስፖርት ኢትዮጵያ ወክሎ በመሳተፍ እና ባንዲራዋን በኦሎምፒክ በመያዝ ቀዳሚው አትሌት ነው።
ገረመው ደምቦባ ታህሳስ 7 ቀን 1925 ዓ.ም በአዲስ አበባ ተወለደ።
እ.አ.አ በ1956 ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ በተሳተፈችበት 16ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በብስክሌት እና አትሌቲክስ ውድድሮች ላይ ተሳትፏል።
በጎዳና ላይ በተደረገ የብስክሌት ግልቢያ ውድድር 24ኛ ደረጃን ይዞ ያጠናቀቀ ሲሆን ያስመዘገበው ደረጃ ከአፍሪካ እና ከእስያ ተፎካካሪዎቹ ቀዳሚ አድርጎታል።
በውድድሩ ላይ ከገረመው በተጨማሪ መስፍን ተስፋዬ፣ ፀሐይ ባሕታ እና መንግስቱ ንጉሴ ተሳትፈዋል።
በጊዜው ኢትዮጵያ በብስክሌት በቡድን አራተኛ እንድትወጣ አስችለዋል።
17ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በጣሊያን ሮም እ.ኤ.አ በ1960 ሲካሄድ ገረመው አሁንም የተካፈለ ሲሆን የሌላ ሀገር ተወዳዳሪዎች በቴክኒካዊ ዘዴ የሚፈጥነውን ጎማ ጫፍ ከኋላ በመንካት የወረወሩት ሲሆን በዚህም ትከሻውና እግሩ ተሰብሮ በሄሊኮፕተር ወደ ሆስፒታል መወሰዱ መረጃዎች ያሳያሉ።
የብስክሌት ቡድኑም በግልም ሆነ በቡድን ውጤት ሳያመጣ ቀረ።
ከጉዳቱ በኋላ ገረመው ወደ አሰልጣኝነት በመምጣት እ.ኤ.አ በ1968 ጃፓን ባዘጋጀችው 19ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች የተካፈለውን ቡድን በአሰልጣኝነት አብሮ ተጉዟል።
እንዲሁም እ.ኤ.አ በ1973 በናይጄሪያ ሌጎስ በተካሄደው ሁለተኛ የመላው አፍሪካ ጨዋታዎች የብስክሌት ቡድን ይዞ በመጓዝ ወርቅ ይዞ ተመልሷል።
ገረመው ደንቦባ ኢትዮጵያ ካፈራቻቸው የብስክሌት ተወዳዳሪዎች ሁሉ ስኬታማ እንደሆነ ይነገርለታል።
በተለያዩ ውድድሮች ተሳትፎ 26 ዋንጫዎች እና 32 ሜዳልያዎች ተሸልሟል።
ኢዜአ እንደዘገበው የታዋቂው እና የአንጋፋው ብስክሌተኛ ገረመው ደንቦባ የቀብር ስነ-ስርዓት ዛሬ በብርሃናተ ዓለም ጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተ-ክርስቲያን ከቀኑ 8 ሰአት ላይ ይፈጸማል።
[ደመቀ ከበደ ፡ አዲስ አበባ]