የአማራ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ የሆኑት አቶ ግርማ የሺጥላ መገደላቸው ተገለጠ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ፣ "ሐሳብን በሐሳብ ማሸነፍ ያቃታቸው አካላት የወንድማችንን የግርማ የሺጥላን ነፍስ ነጥቀዋል" ሲሉ አስታውቀዋል።
ልዩነትን በሰለጠነ መንገድ መፍታት ባሕል በሆነበት ክፍለ ዘመን፣ በሐሳብ የተለየን ሰው ሁሉ በጠብመንጃ ለማሳመን መነሣት የጽንፈኝነት የመጨረሻው ጥግ ነው ሲሉም አስፍረዋል።
"ተወልዶ ባደገበት አካባቢ ፣ ከእኛ የተለየ ሐሳብ ማሰብ አልነበረበትም ብለው የሚያምኑ ነውጠኛ ጽንፈኞች የፈጸሙት አስነዋሪና አሰቃቂ ተግባር፣ ጽንፈኝነትን በጊዜ ታግለን ካላስወገድነው ወደ መጨራረስ እንደሚወስደን ጉልሕ ማሳያ ነው" ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ፣ በመልዕክታቸው መጨረሻም "ነፍስህ በሰላም ትረፍ" ሲሉ ሐዘናቸውን ገልጸዋል።
በሌላም በኩል የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት "የክልሉ መንግሥት የማያዳግም እርምጃ ይወስዳል" ሲል ሚያዚያ 19 ቀን 2015 ዓ.ም ከባሕር ዳር ባወጣው መግለጫ "በዛሬው ዕለት ሚያዚያ 19 ቀን 2015 ዓ.ም ከሰዓት በኋላ የብልፅግና ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ አባል እና የአማራ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ በተከበሩ ግርማ የሺጥላ፣ በግል ጥበቃዎቻቸው እና በቤተሰቦቻቸው ላይ የመንግሥትና የድርጅት ሥራዎችን በአካባቢው ላይ ሠርተው ከመሃል ሜዳ ወደ ደብረ ብርሃን እየመጡ በነበረበት ሰዓት መንዝ ጓሳ ላይ በታጠቁ ኢ-መደበኛ ኃይሎች ጥቃት ተፈጽሟል" በማለት ስለ አሟሟታቸው አስታውቋል።
ምርግለጫው አያይዞም "ግርማ የሺጥላን ጨምሮ እስካሁን በደረሰን መረጃ የአምስት ሰዎች ሕይወት አልፏል፡፡ በደረሰው ልብ ሰባሪ ጥቃት የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት የተሰማውን መሪር ሐዘን እየገለፀ ለቤተሰቦቻቸውና ወዳጆቻቸው እንዲሁም ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ የተሰማውን ጥልቅ ሐዘን ይገልጻል" ብሏል።
"እንዲህ አይነት አጥፊዎች እያደረሱት ያለው መረን የለቀቀ የሽብር ድርጊት ክልሉን እየመራ ያለውን መንግሥትና መላውን ሕዝብ የበለጠ ሊያጠናክር እንጂ በጥፋት ሃይሎች ሴራና ፍላጎት የሚሳካ ምንም አይነት ተልዕኮ የለም፡" ያለው የአማራ ክልላዊ መንግሥት "ስለሆነም ይህንን የሽብር ሥራ እየሠሩ ያሉ እንዲህ አይነት ኃይሎች ላይ የክልሉ መንግሥት የማያዳግም እርምጃ ይወስዳል፡፡ የጥቃቱን አድራሾችም ለሕግ ያቀርባል" ሲል ተከታይ እርምጃዎችን አፅንዖት ሰጥቶ አሳስቧል።