ታዋቂ አትሌቶችን ጨምሮ ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች የተሳተፉበት ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ በአዲስ አበባ ከተማ በድምቀት ተካሂዷል፡፡
ፕሬዝደንት ሳሕለወርቅ ዘውዴ፣ ከንቲባ አዳነች አቤቤና ሻለቃ ኃይሌ ገብረስላሴ ሩጫውን አስጀምረውታል።

ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ በ1994 ዓ.ም በአትሌት ኃይሌ ገብረ ሥላሴ የተጀመረ ሲሆን በአፍሪካ ቀዳሚ በዓለም ደግሞ ስድስተኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ ትልቅ የጎዳና ላይ ሩጫ ነው፡፡
ዛሬ የተካሔደው ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ መነሻው እና መጨረሻው መስቀል አደባባይ ያደረገ ሲሆን አጠቃላይ ርቀቱም 10 ኪሎ ሜትር ነው፡፡
ከዚህኛው ሩጫ ቀደም ብሎ ትናንት የህፃናት ዛሬ ደግሞ የአካል ጉዳተኞች ውድድር ተካሂዷል፡፡

የ 2015 ሶፊ ማልት ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ በዛሬው ዕለት 40,000 ራጮች ታድመውበታል።
በውድድሩ አትሌቶች በ 10 ኪ.ሜ ሩጫ በወንዶች እና በሴቶች ዘርፍ የተወዳደሩ ሲሆን በወንዶች አቤ ጋሻሁን በአንደኝነት፣ ሀይለማርያም አማረ በሁለተኝነትና ገመቹ ዲዳ ደግሞ በሶስተኝነት ውድድሩን አጠናቀዋል። አቤ ጋሻሁን በታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ውድድር ሲያሸንፍ የዘንድሮው ለሶስተኛ ጊዜ ነው።
በሌላ መልኩ ደግሞ ትዕግስት ከተማ ቀዳሚ ሆና ስታጠናቅቅ ፡ መስታወት ፍቅር ሁለተኛ እንዲሁም ፎቴን ተስፋዬ ሶስተኛ በመውጣት የዘንድሮው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የሴቶች ዘርፍ አሸናፊዎች መሆናቸው ታውቋል።
[ ደመቀ ከበደ ፡ አዲስ አበባ ]

