የኢትዮጵያ ሕብረ-ባሕል ለሰብዓዊ መብቶች ድርጅት (ኢሕሰመ) ኖቬምበር 17, 2020 ባወጣው መግለጫ ለዓለም አቀፍ ድርጅቶችና ማኅበረሰባት ጥሪ አቅርቧል።
ድርጅቱ በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ ውስጥ በፌዴራል መንግሥቱና በሕወሓት ተዋጊ ወታደሮች መካከል በትግራይ እየተካሔደ ያለውን ጦርነት አስመልክቶ "ኢሕሰመ ዓለም አቀፍ ድርጅቶችና ማኅበረሰባት ከኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት ጋር አብረው በመቆም ድጋፍ እኒያደርጉ ጥሪ ያቀርባል" ብሏል።
አያይዞም መቀመጫው ሲድኒ - አውስትራሊያ የሆነው ኢሕሰመ በድርጅቱ እምነት በመንግሥት በኩል የሚካሔደው እርምጃ ሕግና ሥርዓትን ከማስከበር አኳያ እንደሆነ ገልጦ ሕወሓት ለፍትሕ እንዲቀርብ ሲል ጥሪውን አሰምቷል።
መቀመጫው ሜልበር - አውስትራሊያ የሆነው የኢትዮጵያውያን - አውስትራሊያውያን የሰላምና የትብብር አድቮካሲ ግሩፕ በበኩሉ "የኢትዮጵያን አንድነትና ህልውና ለማስከበር መንግሥት የሚያደርገውን ጥረት በሙሉ ልብ እንደምንደግፍና የበኩላችንን አስተዋጽኦ ለማድረግ ዝግጁነታችንን ስንገልጽ በታላቅ ኢትዮጵያዊ ኩራት ነው" ብሏል።
በታካይነትም ኢትዮጵያ 'በሕወሓት አመራሮች የተጫነባትን የዘመነ መሳፍንት ዓይነት የጎሳ ፖለቲካ' ማስወገድ ግድ እንደሚላት ጠቁሞ "ኢትዮጵያ ከዚህ በኋላ በመብት ስም አዲስ የጎሳ ጋሻ ጃግሬዎች የሚፈነጩባት አገር ከቶ መሆን የለባትም። ለዚህም ትክክለኛው አማራጭ ወያኔዎችና ግርፎቻቸው የነደፉትና የተገበሩት ፀረ-አንድነትና ፀረ-ሕዝብ ሕገ መንግሥት ሲቀየርና ማንኛውም ኢትዮጵያዊ የጎሳ አጥር ሳያግደው አገሬ ብሎ የሚኖርባት ኢትዮጵያ ስትኖር ብቻ ነው" ሲል አፅንዖት ሰጥቷል።
የኢትዮጵያውያን - አውስትራሊያውያን የሰላምና የትብብር አድቮካሲ ግሩፕ አይያዞም "መንግሥት ከድል ባሻገር ፓለቲካውን ሥልጡን የማድረግና የጎሳ ፖለቲካን ሥር የሚነቅል ቆራጥና ተከታታይነት ያለው እርምጃ እንደሚወስድ ይጠበቃል። ይህ ካልሆነ ግን ወደ ሌላ የጦርነት አዙሪት ላለመግባታችን ምንም ዋስትና የለም" በማለት አሳስቧል።
በፌዴራል መንግሥቱና በሕወሓት በኩል እየተካሄደ ባለው ጦርነት ሳቢያ በአማካይ 4,000 ኢትዮጵያውያን ከትግራይ የሱዳንን ድንበር አቋርጠው ወደ ስደተኞች መጠለያ እየዘለቁ መሆኑን የተባበሩት መንግሥታት ከፍተኛ የስደተኞች ኮሚሽን አስታውቋል።