"ቢበዛ ከ10-15 ቀናት ቢፈጅብን ነው። የሞቱትንም የተማረኩትንም ለሕዝብ እንገልጣለን" - ብ/ጄኔራል ተስፋዬ አያሌው

*** "ባሕር ማዶ መኖራችን ኢትዮጵያዊነታችንን ቅንጣት አይቀረውም፤ ምናልባትም ይጨምረው ይሆናል እንጂ" - አቶ ተስፋዬ እንደሻው

Community

Source: SBS Amharic

በአውስትራሊያ የኢትዮጵያ ኤምባሲ፣ የኢትዮጵያና ኒውዝላንድ የማኅበረሰብ አባላት አማካኝነት "ለአገር ሞታችኋል፤ ምስጋና ያንሳችኋል" በሚል መሪ ቃል ለኢትዮጵያ የአገር መከላከያ ሠራዊት ምሥጋና ለማቅረብ ዛሬ እሑድ ዲሴምበር 3 - 2021 የበይነ መረብ ውይይት ተካሂዷል።

በውውይቱ ላይ የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር ደኤታ አምባሳደር ብርቱካን አያኖ፣ የአገር መከላከያ ሠራዊት ሚኒስትር ደኤታ ወ/ሮ ማርታ ሉዊጊ፣ የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ኤጄንሲ ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ ሰላማዊት ዳዊትና የመከላከያ ሠራዊት ዘመቻ መምሪያ ዋና ኃላፊ ብርጋዲየር ጄኔራል ተስፋዬ አያሌው በተጋባዥ እንግድነት ተገኝተዋል።

ስብሰባውን በንግግር የከፈሉት አቶ በሪሁን ደጉ፤ በአውስትራሊያ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ባለ ሙሉ ሥልጣን ሚኒስትርና ምክትል ሚስዮን መሪ የዕለቱን ፕሮግራም በማስተዋወቅ አስጀምረዋል። በስብሰባው ታዳሚዎችም የአንድ ደቂቃ የኅሊና ፀሎትም ተደርጓል። 
Beryihun Degu
Beryihun Degu Source: SBS Amharic
አቶ በሪሁን በማያያዝም ለውጡ ካስገኛቸው ትሩፋቶች አንዱ በአውስትራሊያና ኒውዝላንድ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ካንብራ ከሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ጋር ያላቸው ግንኙነት መነቃቃትና መሻሻል እንደሆነ ገልጠው፤ የማኅበረሰባቱ አባላት ለኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ፣ ለታላቁ ሕዳሴ ግድብ በገንዘብና በሙያ ያበረከቱትን አስተዋፅዖ በአብነትነት በመንቀስ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።  

ከተጋባዥ እንግዶች በቀዳሚነት ንግግር ያደረጉት የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ኤጄንሲ ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ ሰላማዊት ዳዊት "የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ኤጄንሲ መቋቋም አንዱ የኢትዮጵያ መንግሥት በተቻለ መጠን እያደረገ ያለው የዜጋ መር ዲፕሎማሲ ማሳያ" እደሆነ ገልጠዋል። ለማኅበረሰቡ አባላት ባስተላለፉት መልዕክትም "አንድነታችሁን ጠብቃችሁ፤ በችግር ጊዜ ብቻ ሳይሆን ለልማቱም በጋራ በመቆም የበለጠ ሥራ እንደምትመሩ እምነት አለኝ" ብለዋል።
Selamawit Dawit
Selamawit Dawit Source: SBS Amharic
የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር ደኤታ አምባሳደር ብርቱካን አያኖ፤ "ኤምባሲውና በአካባቢው ያሉ የማኅበረሰብ አባላት ያደረጉትን የመድረክ ዝግጅት በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርና በራሴ ስም አመሰግናለሁ" በማለት ጀምረዋል።
Ambassador Birtukan Ayano
Ambassador Birtukan Ayano Source: SBS Amharic
አክለውም፤ በአውስትራሊያና ኒውዝላንድ የሚገኙ የማኅበረሰቡ አባላት ለኮቨድ-19፣ ለኅዳሴ ግድብ አሁንም በሰብዓዊ ድጋፍ በኩል ያደረጉት አስተዋፅኦዎችን በመጥቀስ "እጅግ በጣም ነው የምንኮራባችሁ" በማለት ምስጋናና አድናቆታቸውን ገልጠዋል።  

የአገር መከላከያ ሠራዊት ሚኒስትር ደኤታ ወ/ሮ ማርታ ሉዊጊም በበኩላቸው "አገራዊ አንድነታችንን በሚያስጠብቅ፣ ሕዝባዊ አንድነታችንን በሚያስከብር መልኩ ከጎናችን በመቆማችሁ እናመሰግናለን። የሞራል ድጋፋችሁ ለሠራዊታችን ስንቅ ነው፤ ለዚያም ትልቅ አክብሮት አለን" ካሉ በኋላ አጋጣሚውን ተጠቅመው "መንግሥት በሚያደርገው ጥሪ መሠረት በሰብዓዊ አገልግሎት፣ በልማትና በሙያዊ ድጋፋችሁን እንድታደርጉልን ጥሪዬን አቀርባለሁ" ብለዋል።
Marta Luwigi
Marta Luwigi Source: SBS Amharic
የመከላከያ ሠራዊት ዘመቻ መምሪያ ዋና ኃላፊ ብርጋዲየር ጄኔራል ተስፋዬ አያሌው ለማኅበረሰቡ አባላት ባደረጉት ገለጣ " [የሕወሓት] የክልል ቢሮ ኃላፊና በሚኒስትር ደረጃ የነበሩ ከ10-12 የሚደርሱ እጃቸውን ሰጥተዋል። ተፈላጊዎቹ [የአመራር አባላት] የሚገኙት ተምቤን በረሃ ውስጥ ነው ያሉት። ሠራዊቱ 'እነሱን ሳንይዝ እንመለስም' በማለት 360 ዲግሪ እየፈተሸ ነው።  ሕ ብለዋል።
Tesfaye Ayalew
B/General Tesfaye Ayalew Source: SBS Amharic
ንግግራቸውንም ሲያጠቃልሉ "የእናንተ ጥረትና ድጋፍ ሠራዊቱ በጣም ደስተኛ ሆኖ ግዳጁን እንዲወጣ ስላደረገው ትልቅ ሚና አለው። ከልብ ምስጋናዬን አቀርባለሁ" በማለት ተናግረዋል።  

በመቀጠልም፤ በአውስትራሊያና ኒውዝላንድ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ማኅበረሰብ አባላትን በመወከል የቪክቶሪያ ኢትዮጵያውያን ማኅበረሰብ ማኅበር ፕሬዚደንት አቶ ተስፋዬ እንደሻው ሲናገሩ "ባሕር ማዶ መኖራችን ኢትዮጵያዊነታችንን ቅንጣት አይቀረውም፤ ምናልባትም ይጨምረው ይሆናል እንጂ" ብለዋል።
Tesfaye Endeshaw
Tesfaye Endeshaw Source: SBS Amharic
በማከልም የማኅበረሰብ አባላቱ ለኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ መከላከያ፣ ለሕዳሴ ግድብ ግንባታና ለአገር መከላከያ ሠራዊት መርጃ ያበረከቱትን የገንዘብና የሙያ አስተዋፅኦዎች በመዘርዘር ገልጠዋል።

ከንግግሩ ማብቂያ በኋላም ከማኅበረሰብ አባላቱ፤

  • ጥፋተኞች ለፍርድ የሚቀርቡት እንዴት ነው?
  • ሕወሓት አሸባሪ ተብሎ ያልተፈረጀው ለምንድነው?
  • ሰላምና ጸጥታ በሌለበት ምርጫን እንዴት ማካሔድ ይቻላል?
  • ሕግ የማስከበሩ እርምጃ ምን ያህል ተሳክቷል?
  • ስለ ተያዙት፣ የተደመሰሱትና ያመለጡት ይፋ የማይደረገው ለምንድነው? የሚሉና በጎሳ የተደራጀው የልዩ ኃይልና ሚሊሺያ ሠራዊት አባላት የወደፊት ዕጣ ፈንታ የተመለከቱ ጥያቄዎች ቀርበዋል።
ጥያቄዎችን አስመልክቶ ተጋባዥ እንግዶቹ ምላሽ የሰጡ ሲሆን፤

ብርጋዲየር ጄኔራል ተስፋዬ በሰጡት ምላሽ "አሁን ያለው ሠራዊት የጎሣ ሠራዊት አይደለም። ኢትዮጵያ ሠራዊት ነው። የሚዋደቀው ለጎሣውና ለመንደሩ አይደለም። በግሌ የክልል ልዩ ኃይል አያስፈልግም የሚል አቋም አለኝ። እንደ ተቋም ገና አልተነጋገርንበትም። ከአብዲ ኢሌ መማር አለብን። የአማራ ክልል ባለስልጣናት የተገደሉት በክልል ልዩ ኃይል ነው። ከፖሊስ ኃይል ጋር ቢቀላቀል ጥሩ ነው። ክልል ኃይል የሚባል ነገር ሊኖረው አይገባም የሚል አቋም ነው ያለኝ" ብለዋል።

የመከላከያ ሚኒስትር ደኤታ ማርታ በበኩላቸው " የፀጥታ ኃይሉን በሚመለከት የክልልና ፌዴራልን አስመልክቶ የተናበበ አሠራር ለማካሔድ ጥናቶች እየተካሔዱ ነው። የጥናቱ ውጤት እንዳበቃም ማስተካከያ የሚደረግ ይሆናል። ይህን አስመልክቶ በመንግሥት በኩል ግንዛቤ አለ" ብለዋል።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደኤታ ብርቱካንም "አንድን ድርጅት በአሸባሪነት ለመፈረጅ የራሱ የሆነ ሂደት ስላለው በሂደት የሚወሰን ይሆናል። ቀዳሚው ጉዳይ ሕግን የማስከበሩ እርምጃ ነው" ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።

 

 

  

 


Share

Published

Updated

By Kassahun Seboqa Negewo

Share this with family and friends


Follow SBS Amharic

Download our apps
SBS Audio
SBS On Demand

Listen to our podcasts
Independent news and stories connecting you to life in Australia and Amharic-speaking Australians.
Ease into the English language and Australian culture. We make learning English convenient, fun and practical.
Get the latest with our exclusive in-language podcasts on your favourite podcast apps.

Watch on SBS
SBS World News

SBS World News

Take a global view with Australia's most comprehensive world news service