በጎንደር ከተማ ሚያዝያ 18 ከተከሰተው ግጭት ጋር ተያይዞ 373 ሰዎች በሕግ ቁጥጥር ስር መዋላቸውን የአማራ ክልል ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ ደሳለኝ ጣሰው ትናንት ሚያዝያ 21/2014 በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አስታወቁ።
የፀጥታ ኃላፊው ለአካባቢው ብዙኅን መገናኛ እንደገለጡት ተፈላጊ ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር እስኪውሉ ድረስ በጎንደር ከተማ አስተዳደር የሰዎችንና ተሽከርካሪዎችን እንቅስቃሴ ለመገደብ ከምሽቱ 1:00 ሰዓት ጀምሮ የሰዓት ዕላፊ ገደብ መጣሉን ገልጠዋል።
አክለውም፤ ከፀጥታ ኃይላት በስተቀር የፀጥታ ኃይላትን መደበኛ ልብስ ለብሶና መሣሪያ ታጥቆ መገኘት እርምጃ እንደሚያስወስድ አስጠንቅቀዋል።
ከተማይቱን ለቅቀው የሚወጡም ሆነ የሚገቡ መሣሪያዎች እንዳይኖሩ ዕገዳ መጣሉን አስታውቀዋል።
የግል ትጥቆች ያሏቸው ፋኖዎች ከመንግሥት ስምሪት እስከሚሰጣቸው ድረስ በቀዪአቸው ሆነው እንዲጠባበቁ አሳስበው፤ በፋኖ ስም ለመነገድ የሚሞክሩ አካላት ላይ ጥብቅ እርምጃ እንደሚወሰድ አስጠንቅቀዋል።
ለግጭቱ መከሰት ማኅበራዊ ሚዲያን አካትቶ ውስጣዊና ውጪያዊ አስባቦች መኖራቸውን የገለጡት አቶ ደሳለኝ፤ ከ20 በላይ የንግድና የመኖሪያ ቤቶ መጋያታቸውንና 11 ቤቶች በከፊል ወይም ሙሉ በሙሉ መዘረፋቸውን ጠቅሰዋል።
በግጭቱ ሳቢያም ከሁለቱም የክርስትናና እስልምና እምነት ተከታዮች በኩል የ14 ሰዎች ሕይወት ማለፉንና 118 ሰዎች ለመለስተኛና ከባድ ቁስል አደጋ መዳረጋቸውም ተነግሯል።
በግጭቱ ወቅት ኃላፊነታቸውን በቅጡ ያልተወጡ የፀጥታና የፖለቲካ መሪዎች በሕግ ተጠያቂ እንዲሆኑ መደረጉንም አቶ ደሳለኝ አስታውቀዋል።
የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥትም በዕለቱ ሚያዝያ 18 ባወጣው መግለጫ ስለ ግጭቱ መከሰት ሲገልጥ "በዛሬው ዕለት የጎንደር ከተማ ነዋሪ እና የጎንደር ሕዝበ ሙስሊምና ሕዝበ ክርስቲያኑ እንዲሁም የኹሉም አባት የነበሩት ታላቁ ሸኽ ከማል ለጋስ ሥርዐተ ቀብር እየተፈጸመ በነበረበት ሰዓት ከቀብር ቦታው ጋር ድንበርተኛ የኾነው ቤተ ክርስቲያን ላይ ለቀብር የሚሆን ድንጋይ “እናነሳለን የመስጊዱ ክልል ነው፤ አታነሱም የቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር ነው” በሚል በተወሰኑ ግለሰቦች መካከል በተጀመረ ግጭት የሰው ህይወት ጠፍቷል፤ የአካል ጉዳትም ደርሷል። የተለያዩ ንብረቶችና ተቋማትን የማጥፋት እንቅስቃሴዎችም ተስተውለዋል" ማለቱ ይታወሳል።

