የአፍሪካ ሕብረት ሊቀ መንበር ኢትዮጵያ ውስጥ እየተካሄደ ያለውን ግጭት ለመፍታት ልዩ የልዑካን ቡድን ሰየሙ

*** ፕሬዚደንት ሳህለወርቅ ዘውዴ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ልዑክነት ከወቅቱ የአፍሪካ ሕብረት ሊቀመንበርና የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚደንት ጋር ተወያዩ

African Union

South African President Cyril Ramaphosa Source: AP

የወቅቱ የአፍሪካ ሕብረት ሊቀመንበርና የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚደንት ሲሪል ራማፎሳ በኢትዮጵያ መንግሥትና በሕወሓት መካከል እየተካሄደ ያለውን ጦርነት በውይይት ለመፍታት እንዲያስችል ሶስት የቀድሞ አፍሪካ አገራት መሪዎችን ያቀፈ አንድ ልዩ ልዑካን ቡድን መሰየማቸውን የአፍሪካ ሕብረት ሊቀመንበር ቢሮ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።

የልዑካን ቡድኑ አባላት ዮኣኪም ቺሳኖ - የቀድሞ የሞዛምቢክ ፕሬዚደንት፣ ኤለን ጆንሰን-ሲርሊፍ የቀድሞ ላይቤሪያ ሪፐብሊክ ፕሬዚደንትና ኬጋሌማ ሞትላንቴ ናቸው።

ይህ በእንዲህ እንዳለም የኢትዮጵያ ፕሬዚደንት ሳህለወርቅ ዘውዴ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ልዩ ልዑክ ሆነው ደቡብ አፍሪካ ተገኝተው ትግራይ ውስጥ ተከስቶ ስላለው ግጭት ሁኔታ ለፕሬዚደንት ራማፎሳ ገለጣ አድርገዋል።   

ፕሬዚደንት ራማፎሳ በበኩላቸው እንደ አፍሪካ ሕብረት ሊቀመንበርነታቸውና የአፍሪካ ሕብረት አባል አገራት ቤተሰብነታቸው ተቀስቅሶ ያለው ግጭት ጥልቅ ስጋት ያሳደረባቸው መሆኑንና በሁለቱ ወገኖች መካከል በሚካሄድ ውይይት ከዕልባት ላይ እንዲደርስ ያላቸውን ብርቱ ፍላጎት ለፕሬዚደንት ሳህለወርቅ ገልጠዋል። 

አያይዘውም ለግጭቱ ዕልባት ማበጃ የሚያግዝ ሶስት የቀድሞ የአፍሪካ አገራት መሪዎችን የአፍሪካ ሕብረት ልዩ የልዑካን ቡድን አባላት አድርገው መሰየማቸውንና በዚሁ መንፈስም በቀጣይ ቀናት ውስጥ ልዑካኑ እህት ወደ ሆነችው ኢትዮጵያ እንደሚጓዙ ተናግረዋል።   

የልዩ ልዑካኑ ቀዳሚ ተግባርም በግጭቱ ውስጥ ካሉ ወገኖች ጋር ሁሉ ግጭቶቹ የሚቆሙበትን፣ በአካታች ብሔራዊ ውይይት ለግጭቱ አስባብ የሆኑ ጉዳዮች ዕልባት የሚያገኙበት፣ ሰላምና መረጋጋትን ዳግም በኢትዮጵያ ማስፈን እንደሆነ የሕብረቱ ሊቀመንበር መግለጫ አስታውቋል።   

መግለጫው አክሎም፤ የሊቀመንበሩ ተነሳሽነት አፍሪካን ከግጭት ነፃ ለማድረግ "የጠመብንጃዎችን ላንቃ ፀጥ ማሰኘት" እና "አፍሪካዊ መፍትሔዎች ለአፍሪካዊ ችግሮች" ከሚለው የአፍሪካ ሕብረት ዓላማ ጋር የተያያዘ እንደሆነ አመልክቶ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድም ይህንኑ ተነሳሽነት በመቀበል ለልዩ ልዑካን ቡድኑ የኢትዮጵያ መንግሥት ትብብር እንደሚያደርግ ማረጋገጣቸውን ያደነቁ መሆኑን አንስቷል።

በተያያዥነትም ፕሬዚደንት ሳህለወርቅ አሁን ተከስቶ ላለው ግጭት ታሪካዊ መንስኤዎቹን ማስረዳታቸውንና ፕሬዚደንት ራማፎሳም የፕሬዚደንቷን ገለጣ በመልካም ጎኑ መቀበላቸውንም መግለጫው አስታውቋል።  

ይህ በእንዲህ አንዳለም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መረጃ ማጣሪያ ባወጣው ማስተባባያ "የፌዴራል መንግሥት ከሕወሓት ቡድን ጋር ሊደራደር ነው በሚል የተሰራጨው ወሬ ሃሰት ነው" በማለት አስታውቆ ሆኖም "ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የአፍሪካ ሕብረት ሊቀ መንበር የሆኑትን የሲሪል ራማፎሳ ልዑካን ተቀብለው በግል ይወያያሉ" ብሏል።

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መረጃ ማጣሪያ በመቋጫነት "ድርድርን አስመልክቶ የፌዴራል መንግሥት ያለው አቋም ፈጽሞ ያልተለወጠ ነው" ሲል አስታውቋል።

 

 


Share

Published

Updated

By Kassahun Seboqa Negewo

Share this with family and friends


Follow SBS Amharic

Download our apps
SBS Audio
SBS On Demand

Listen to our podcasts
Independent news and stories connecting you to life in Australia and Amharic-speaking Australians.
Ease into the English language and Australian culture. We make learning English convenient, fun and practical.
Get the latest with our exclusive in-language podcasts on your favourite podcast apps.

Watch on SBS
SBS World News

SBS World News

Take a global view with Australia's most comprehensive world news service