የአውስትራሊያ 2026 ሕዝብ ቆጠራ ማክሰኞ ኦገስት 11 / ነሐሴ 5 ይከወናል። በዕለተ ምሽቱ ማንኛውም አውስትራሊያ ውስጥ ያለ ሰው በሙሉ የግድ ሊቆጠር ይገባል። የሕዝብ ቆጠራ ዳታ የት እንደምንኖር፣ ቤት ውስጥ የምንናገራቸው ቋንቋዎች ምን እንደሆኑ፣ ድጋፍ ለማድረግና አውስትራሊያ እንደ ሀገር እንደምን በመለወጥ ላይ እንዳለች ለመገንዘብ ይረዳል። መቆጠርዎ ማኅበረሰብዎ፣ ባሕልና እምነቶችዎ ውክልናን ስለማግኘታቸው ለማረጋገጥ ያግዛል። የቤትዎ ነዋሪዎች የሕዝብ ቆጠራን ሞልተው ስለማጠናቀቃቸው ማወቅ ግድ የሚልዎትን እነሆን።
Key Points
- ኦገስት 11 - 2026 ምሽት አውስትራሊያ ውስጥ የሚገኙ ማናቸውም ሰዎች በሕዝብ ቆጠራ ለመሳተፍ ግድ ይሰኛሉ
- መልሶችዎ አገልግሎት ሰጪዎች የሚያሻዎትን እንዲረዱና እኒያ አስፈላጊ ፍላጎቶችም እንደምን ወደፊት ሊለወጡ እንደሚችሉ ግንዛቤ እንዲጨብጡ ያግዟቸዋል
- እርስዎ ያጋሩት ማንኛውም ግለ መረጃ በጥብቅ ተጠብቆ ይያዛል፤ እርስዎን በሚያመላክት ሁኔታ አይሰራጭም።
- የሕዝብ ቆጠራ ዳታ የእርስዎ ማኅበረሰብ ስለሚያገኛቸው አገልግሎቶችና ድጋፎች ከውሳኔ ላይ ለመድረስ ግንዛቤን ያስጨብጣል
የሕዝብ ቆጠራ ፋይዳ ሰዎችን መቁጠር ብቻ ነውን?
በየአምስት ዓመቱ የአውስትራሊያ ስታቲስቲክስ ቢሮ አውስትራሊያ ውስጥ ያሉ የእያንዳንዱን ቤት ነዋሪዎች ይቆጥራል። ይህ የሕዝብና ቤት ቆጠራ፤ በደፈናው የሚታወቀው ሕዝብ ቆጠራ በሚል ነው።
የሚሰበሰበው መረጃ ቀዬዎ ወይም ማኅበረሰብዎ የሚያገኟቸውን አገልግሎቶች ለመቅረፅ ያግዛል።
የአውስትራሊያ ስታቲስቲክስ ቢሮ ሀገር አቀፍ ቃል አቀባይ፤ ኤሚሊ ዎልተር የሕዝብ ቆጠራው አውስትራሊያ ውስጥ ግዙፉ የዳታ ስብስብ እንደሆነና የሀገሪቱን የተወሰኑ ወሳኝ ጠቃሚ ስታቲስቲክን አቅራቢ እንደሁ ተናግረዋል።
“የእኛ ቅንጭብ ማንነት ነው … ሲልም በጊዜ ሂደት እንደምን እየተለወጥን እንዳለን አመላካች ነው” ብለዋል። “የሕዝብ ቆጠራው ስለ ጤና፣ ትምህርት፣ ባሕላዊ ማንነትና ሥራን አስመልክቶ ይጠይቃል፤ ያም የአውስትራሊያን የዳበረ ምጣኔ ሃብታዊ፣ ማኅበራዊና ባሕላዊ ገፅታ አንፀባራቂ ነው” ሲሉም አክለዋል።
የሕዝብ ቆጠራ ተገቢ አገልግሎቶችና መሠረተ ልማቶች፤ ለግለሰቦችና ማኅበረሰባት በሚሿቸው ወቅት እንዲያገኙ ለማስቻል አጋዥ ነው። ይህም፤ የቋንቋ አገልግሎቶችን፣ ትምህርት ቤቶችን፣ የጤና ክብካቤዎችን፣ የማኅበረሰብ ፕሮግራሞችን፣ የሕዝብ ትራንስፖርትና የሠፈራ ድጋፎችን አካታች ነው።

የሕዝብ ቆጠራውን የግድ መሙላት ያለበት ማን ነው?
እያንዳንዱ አውስትራሊያ ውስጥ የሚገኝ ግለሰብ ማክሰኞ ኦገስት 11, 2026 የሕዝብ ቆጠራ ምሽት የመቆጠር ግዴታ አለበት።
የሕዝብ ቆጠራን መከወን ግዴታ ነው። ይህም ማለት የእያንዳንዱ መኖሪያ ቤት ነዋሪ በሕዝብ ቆጠራ መዝገብ ላይ መሥፈር አለበት።
“ያም ዓለም አቀፍ ተማሪዎችን፣ ጎብኚዎችን፣ የቪዛ ባለቤቶችንና ሕፃንትን ሁሉ ያጠቃልላል። የተወሰኑ ሰዎች ሕፃናትን በሕዝብ ቆጠራ ፎርም ላይ ሳያሠፍሩ ይቀራሉ” በማለት ወ/ሮ ዎልተር ልብ ያሰኛሉ።
በሕዝብ ቆጠራ ምሽት የቤትዎን ነዋሪዎች ምዝገባ ሲያከናውኑ፤ በዕለተ ምሽቱ እርስዎ ቤት ውስጥ ያሉትን በሙሉ አካትተው ፎርሙ ላይ ሊያሠፍሩ ይገባል።
በሕዝብ ቆጠራ ምሽት እቤት ውስጥ ባልኖርስ?
በኦገስት 11/ ነሐሴ 5 ባሕር ማዶ ከሆኑ ፎርሙን መሙላት አይጠበቅብዎትም።
ይሁንና አውስትራሊያ ውስጥ በጉዞ ላይ ካሉ ግና፤ ለምሳሌ ያህል ካምፕ ወይም ወዳጆችዎ ዘንድ ከሆኑ፤ የትም ይሁኑ የት የሕዝብ ቆጠራውን ሊያጠናቅቁ ይገባዎታል። የሕዝብ ቆጠራው የት እንደሚኖሩ የሚያነሳ መጠይቅ አለው።
የቆጠራ ፎርሙን የግድ በዕለቱ ማጠናቀቅ አይጠበቅብዎትም፤ ሆኖም በትክክል ኦገስት 11, 2026 ምሽት የት እንደነበሩ ማሥፈር ግና ይጠበቅብዎታል። በሕዝብ ቆጠራ ምሽት የት እንደሚሆኑ በእርግጠኛነት ካወቁም ቀደም ብለው ፎርሙን ሞልተው ማጠናቀቅ ይችላሉ።
የምጠየቀው ጥያቄዎች ምንድን ናቸው?
የሕዝብ ቆጠራ ምሽት ከመድረሱ በፊት፤ አብዛኛዎቹ መኖሪያ ቤቶች የሕዝብ ቆጠራ ፎርሙን እንደምን ኦንላይን ላይ መሙላት እንደሚችሉ የሚያብራራ ደብዳቤ ይደርሳቸዋል። የተወሰኑቱ የሚደርሳቸው የወረቀት ፎርም ይሆናል።

ወ/ሮ ዎልተር፤ የሕዝብ ቆጠራው ስለ ጤና፣ ትምህርት፣ ሥራና ሌሎችም በጋራ ስለ ነዋሪዎችና ማኅበረሰብ ሰፋ ያለ ገፅታን አመላካች እንደሚሆን አመላክተዋል።
“አንድ ግለሰብ የአቦርጂናል እና ቶረስ ሰርጥ ደሴት ተወላጅ ስለመሆንና አለመሆን፣ ቤት ውስጥ የሚናገረው ቋንቋ፣ የእራሱ ትውልድ ሀገርና የቤተሰቦቹ ትውልድ ሀገር፣ ዝርያ፣ ሃይማኖት፣ አውስትራሊያ የገባበት ቀንን የመሳሰሉ ጥያቄዎች አሉ” ሲሉ በማያያዝ ገልጠዋል።
የእኔ የግል መረጃ በምን ሁኔታ ለጠቀሜታ እንደሚውል ስጋት ካለኝስ?
ግለ መረጃዎን ለመጠበቅ ግብር ላይ ያሉ አፈፃፀሞች አሉ።
የሕዝብ ቆጠራው ስለ ግለሰቦች አይደለም፤ ጠቅላላ ሕዝብ ተኮር መረጃ ላይ እንጂ።
የሕዝብ ቆጠራው የዳታ ጥራት ደረጃን ለማገዝ ያልተዛነፈ የተለያዩ አካባቢዎችን አክሎ ስምዎንና አድራሻዎን ይጠይቃል። ስሞች በሂደቱ ውስጥ ቀደም ብለው ከሌሎች ዝርዝር መረጃዎች ይለያሉ።
በሕግ የሕዝብ ቆጠራ ዳታን ለማንም እንድናጋራ አይፈቀድልንም፤ ለማረጋገጫነት ካልሆነ በስተቀር። ለማንኛውም መንግሥታዊ ኤጄንሲ ጭምር።ኢሚሊ ዎልተር
ይህም ማለት እርስዎ የሰጡት መረጃ በምስጢር የሚያዝ ይሆናል፣ በጥብቅ የሚቀመጥና የእርስዎን ማንነት የሚያጋልጥ አይሆንም። ከመንግሥት መሥሪያ ቤቶች ከአውስትራሊያ ስታቲስቲክ ቢሮ በስተቀር እርስዎ ጨምሮ የተካተቱበት የሕዝብ ቆጠራ ፎርም በማናቸውም ድርጅቶች ዘንድ ተደራሽነት አይኖረውም።
ይፋ የሆነ የሕዝብ ቆጠራ ዳታ ለማኅበረሰብ ቡድኖች ፣ አትራፊ ላልሆኑ ድርጅቶች፣ ለንግድና መንግሥታት ጠቀሜታነት ይውላል።
Welcoming Australia አንዱ ድርጅት ነው። በመላ ሀገሪቱ ከአካባቢ መንግሥታት፣ ስፖርት ክለቦች፣ ዩኒቨርሲቲዎችና መሥሪያ ቤቶች ጋር አብሮ ይሠራል።
የድርጅቱ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አሊም ዓሊ፤ የእርስዎ እውነተኛ ምላሽ ስለምን እንደሚያሻ ሲያስረዱ፤
“ቋንቋዎን፣ እምነትዎን፣ ባሕልዎን ካላሠፈሩ የድጎማ ገንዘብ ፈቃጅ በሆኑት ዘንድ ለዓይን የሚገቡ አይሁኑም” ይላሉ።

ለሕዝብ ቆጠራው ያልተዛነፈ ምላሽ የመስጠቱ ጠቀሜታ ምንድን ነው?
ሁሉንም የሕዝብ ቆጠራ ጥያቄዎችን ሳያዛንፉ መመለስ፤ ለትምህርት ቤት፣ የማኅበረሰብ ማዕከል፣ የቋንቋ ድጋፍና ሌሎች ጠቃሚ አገልግሎቶች ዕቅድ ላይ የእራስዎንና የማኅበረሰብዎን ድምፅ ማካተት ነው።
አቶ ዓሊ ሁሉም ሰው ጥያቄዎቹን ሳያዛንፍ እውነተኛ ምላሾችን እንዲሰጥ ያበረታታሉ።
ተሳትፎ ማድረግ ለዕይታ የመብቃት ክብር ነው፤ ማኅበረሰብዎ ለሚገባው አገልግሎት የበጎነት ምንጭ መሆንም ጭምር ነው።አሊም ዓሊ
ፒተር ዱካስ የአውስትራሊያ ዘውጌ ማኅበረሰባት ፌዴሬሽን ምክር ቤት ሊቀመንበር ናቸው።
እንደ ዘውጌ ማኅበረሰባት ምክር ቤት ያሉ ድርጅቶች ከአውስትራሊያ ስታቲስቲክ ቢሮ ጋር የሕዝብ ቆጠራው መረጃዎች በተለያዩ ቋንቋዎች እንዲቀርቡ፣ ማናቸውንም ስጋቶች በቅርርቦሽ ለማንሳት አብሮ የሚሠራ እንደሁ ይናገራሉ።
“ያልተዛነፈ ዳታን ማግኘትና አውስትራሊያ ውስጥ ሰዎች ጥልቅ ግንዛቤን እንዲጨብጡ ማስቻልና ስለ እውነት ጠቃሚ የሲቪክ ማዕከል አካል ነው” ባይ ናቸው።
አሊም ዓሊ "የሕዝብ ቆጠራ ዳታ ለእንኳን ደህና መጣችሁ አውስትራሊያ ሁነኛ ሚና ተጫዋች ነው ... ስለምን፤ የምንሠራለት ድርጅት ይበልጡን ዝንቅ ማኅበረሰባትን ... ተቀባይ፣ አካታችና በላቀ ሁኔታ እንድንሠራ ድጋፍ ያደርግልናል” ሲሉ ተናግረዋል።

የሕዝብ ቆጠራ ዳታ እንደምን ነው መድብለ ባሕል ማኅበረሰባትን የሚያግዘው?
የሕዝብ ቆጠራ በሰዎች ላይ ትልቅ ተፅዕኖ አለው።
እርስዎ የሚያጋሩት መረጃ የማኅበረሰ ቡድናት፣ ንግዶችና መንግሥታት ምን ዓይነት አገልግሎቶች እንደሚያሹና ማኅበረሰብዎም ማግኘት ስላለበት አገልግሎቶች መረጃን መሠረት ካደረገ ውሳኔ ላይ ለመድረስ ያግዛቸዋል።
አሊም ዓሊ፤ የሕዝብ ቆጠራ ዳታ ልክ እንደ ካርታ፤ እንደ ሕዝብ ማን እንደሆን የሚያሳይ ስለመሆኑ ይገልጣሉ።
“ለምሳሌ፤ ዳታ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሰዎች በተወሰነ ሥፍራ ዝቅ ካለ የእንግሊዝኛ ቋንቋ ችሎታ ጋር መኖራቸውን ሲያመላክት፤ ያ መረጃ ... የጤና ክብካቤና የትርጉም አገልግሎቶችን በአካባቢው ባሉ ሆስፒታሎች በተለያዩ ቋንቋዎች እንዲቀርቡ ለመጠቀም ያስችላል። እንዲሁም፤ የተሰወሩ ማኅበረሰባት ብለን ለምንላቸው ልማዳዊ ምክሮችንና የገንዘብ ድጎማዎችን ለማድረግ ለይተን እንድናውቃቸው ይረዳናል” ብለዋል።
ትልቁን ምስል ስንመለከት፤ አውስትራሊያ ውስጥ አያሌ ዝንቅ ማኅበረሰባትን ለመንቀስ በጣሙን ጠቃሚ ነው።
አቶ ዱካስ “ለምሳሌ … ይበልጡን የተደራጁ ማኅበረሰባት ምናልባትም የሚያሿቸው ልዩ ፍላጎቶች አረጋውያንን መርዳት ቢሆን፤ አዲስ በመጡቱ ዘንድ ግና ምናልባትም የቋንቋ ድጋፍ ሲልም መሠረታዊ የሠፈራና ትምህርቤቶች ሊሆኑ ይችላሉ” በማለት ያስገነዝባሉ።

ድጋፍ አለ?
የሕዝብ ቆጠራ ቀን መቃራብን ተከትሎ የአውስትራሊያ ስታቲስቲክ ቢሮ የሕዝብ ቆጠራው በሁሉም ሥፍራ ሰዎች አጠናቅቀው እንዲሞሉ፤ በመላው አውስትራሊያ ካሉ ድርጅቶች፣ ንግዶችና የማኅበረሰብ ቡድናት ጋር ተባብሮ ይሠራል። ይህም የከተማ፣ የገጠርና ሩቃማ ሥፍራዎች ነዋሪ የሆኑትን፣ እንዲሁም፤ በሆቴሎች፣ ሆስፒታሎች፣ ካምፖችና የካራቫን ፓርኮች ያካተቱ ድጋፎች አሉ።
አቶ ዓሊ፤ የአውስትራሊያ ስታቲስቲክ ቢሮ በራሪ ወረቀቶች፣ የኦዲዮ መምሪያዎችንና የቪዲዮ ምንጮችን በተለያዩ ቋንቋዎች ስለማሰራጨቱ ያመላክታሉ።
አክለውም “ሌላው ቀርቶ በግል እገዛን ለማግኘት በየቀዬው ያሉ ሕጋዊ የሆኑ የሕዝብ ቆጠራ ድንኳኖችን መጎብኘት ይቻላሉ፤ በተጨማሪም በስልክ ከሕዝብ ቆጠራ ግንኙነት ማዕከል እርዳታን ማግኘት ያቻልዎታል። አስተርጓሚ የሚሹም ከሆነ እንዲሁ የትርጉምና አስተርጓሚ አገልግሎቶችን መጠቀም ይችላሉ” ብለዋል።
የሕዝብ ቆጠራ ምሽት ማክሰኞ ኦገስት 11 / ነሐሴ 5 መሆኑን ልብ ይበሉ። በእዚያን ምሽት አውስትራሊያ ውስጥ ካሉ መቆጠርዎን እርግጠኛ ይሁኑ። .
ፎርሙን ሞልቶ ለማጠናቀቅ የሚፈጀው ጊዜ አጭር ነው። ይሁን እንጂ የሚሰጡት መረጃ አገልግሎቶችን እማግኘትና ማኅበረሰብዎ ለዓመታት የሚሻውን ድጋፍ እንዲያገኝ ለማስቻል በእጅጉ አጋዥ ነው።
የሕዝብ ቆጠራን አስመልክቶ ተጨማሪ መረጃን ለማግኘት Census website ይጎብኙ። ወይም ከእንግሊዝኛ ውጪ በሆነ ቋንቋ መረጃ ወይም ድጋፍ ለማግኘት Language support page ይጎብኙ።
ይህ ዝግጅት የተሰናዳው ከአውስትራሊያ ስታቲስቲክ ቢሮ ጋር በመተባበር ነው።






