የውልደትና ዕድገት ሽርቦሽ ሆኖ፤ አንበሳ ለጋ ወጣት ሳለ ሙዚቃ - የሕይወት ጥሪው ሆነች።
ለመጀመሪያ ጊዜ መድረክ ላይ እንዲወጣ አጋጣሚውን የፈጠረለት የእናት አገር ጥሪ ድጋፍ ማሰባሰቢያ ዝግጅት ነው። ያኔ የቀበሌ ኪነት ቡድን አባል ነበር።
የአንበሳ የሙዚቃ ጉዞ በቀበሌ ኪነት አልተወሰነም። ወደ ከፍተኛ ከፍ አለ።

ሲልም፤ ወደ ውትድርና ሕይወት አመራ። ይሁንና ውትድርናው ጠብመንጃ እንዲጨብጥ እንጂ ክራሩን ይዞ መድረክ ላይ እንዲገዝፍ ባለመፍቀዱ የውትድርና ሕይወትን እምቢኝ ብሎ ወደ ሲቪል ሕይወቱ አመራ። ይሁንና ያለ ሕጋዊ ስንብት ከውትድርና ዓለም መውጣት “በከጂነት” ያስጠይቃልና የአምስት ዓመት እስራት ተበይኖበት ዘብጥያ ወረደ።
ከእሥር እንደወጣ ያመራው ወደ ቀጣና የኪነት ቡድን ነበር። ብዙም ሳይቆይ ግና የኤርትራ ነፃ አውጪ ግንባር ኤርትራን ሲቆጣጠር እንደሌሎች ኢትዮጵያውያን ሁሉ አሥመራን ለቅቆ ወጣ። አዲግራት - ትግራይ ገባ።
እንደ ኤርትራ ሁሉ ኢትዮጵያም በኢሕዲሪ መንግሥት ግርሰሳ ሳቢያ በኢሕአዲግ መዳፍ ውስጥ ነበረች። አፍላ የነበረው ጉዳይም የሽግግር መንግሥቱን ቻርተር የማጽደቅ ጉዳይ ነበር። እምብዛም ሳይቆይ አሥመራ ሳለ በሙዚቃ ሕይወቱ የሚያውቁት የአዲግራት ቀበሌ ኪነት አባላት እንዲቀላቀላቸው ግብዣ አቀረቡለት። አምበሳም ስለ ቻርተሩ አዲስ ግጥማና ዜማ ከውዝዋዜ ጋር አቀናብሮ እነሆኝ አላቸው።

አዲግራት ላይ ጠቅሎ መስፈር ስላልፈለገ ወደ አዲስ አበባ አቀና። ተክለ ሃይማኖት ሠፈር ካገኛቸው የኤርትራና የትግራይ የኪነ ጥበብ ወዳጆቹ ጋር ሆነው “ወልዋሎ” ባንድን አቆሙ። የሙዚቃ ሕይወታቸውንም መግፋት ጀመሩ።

አንበሳ ወደ አገረ አውስትራሊያ በ2007 ዓ.ም. መጥቶ እስከቀረ ድረስ ኢትዮጵያ ውስጥ የአማርኛ፣ ትግርኛና ትግረ ታዋቂ ድምጻውያንን በመድረክና በስቱዲዮ ካሴት ቀረጻ አጅቧል።
በአውስትራሊያ ሕይወቱም ከቤተሰቡ ድጋፍ ጋር ከሙዚቃ ሥራው አለተለየም።

የሙዚቃ ሕይወቱን በምልሰት ተመልክቶ ለትግርኛ ሙዚቃ ያበረከታቸውን አስተዋጽዖዎቹን ሲገልጥ ያለው “ ለትግርኛ ሙዚቃ ከፍተኛ አስተዋጽዖ አድርጌያለሁ። የትግሪኛ ሙዚቃ አሁን ላለበት ዕድገት የእኔ እጅ አለበት። በዚያም እኮራለሁ” የሚል ነው።





