Key Points
- የጎንደር ተፈጥሯዊና ባሕላዊ ሃብቶች
- ጥሪ ለባሕር ማዶ ነዋሪ ኢትዮጵያውያን
- የበዓለ ጥምቀት መሰናዶና የቅርሶች ጥገና
በአቶ ቻላቸው ገለጣ መሠረት፤ እ.ኢ.አ. በ1996 ዓ.ም ጎንደር ስድስት ሺህ ጎብኚዎችን አስተናግዳለች። ከጎብኚዎቹ 70 ፐርሰንቱ የውጭ ቱሪስቶች ነበሩ።
ሆኖም፤ በ2011 የውጭ ቱሪስቶች ቁጥር ወደ 26 ሺህ ለመድረስ በቅቷል። በ2014 ግና ወደ 532 አሽቆልቁሏል።
በአንፃሩ በ2013 የአገር ውስጥ ቱሪስቶች ቁጥር 57ሺህ ሲደርስ፤ በ2014 ወደ 326 ሺህ ለማሻቀብ ችሏል።
በውጭና በአገር ውስጥ መካከል ያለውን የቱሪስቶች ቁጥር መዋዠቅ አካክሶ ለማስከንና ለማጎልበት "የውጭ አገሩ ቱሪዝም ሲወድቅ አብሮ የሚወድቅ የአገር ውስጥ ቱሪዝም ኢኮኖሚ እንዳይኖር፤ የአገር ውስጥ ቱሪዝም ላይ በርትተን እየሠራን ነው" ሲሉ አቶ ቻላቸው ተናግረዋል።
ለቱሪዝም ኢንዱስትሪው ማጠናከሪያነት አንዱ ብልሃት ኩነቶችን መፍጠር እንደሆነ ያመላከቱት አቶ ቻላቸው፤ በቡርቋስ የሙዚቃ መንደር የአዝማሪ ፌስቲቫል ለማድረግ ውጥን ተይዞ እንዳለ ገልጠዋል።

ስለ ጎንደር የቱሪዝም መስህቦች አስመልክተውም፤ ጎንደር ከተማ ውስጥ ስላሉ ዐቢያተ ክርስቲያናት፣ ዐቢያተ መንግሥታት፣ ከ40 እስከ 60 ኪሎ ሜትሮች ባሉ ርቀቶች ውስጥ የጣና እንሰሳትና ዕፅዋቶችና ገዳማት፤ በ100 ኪሎ ሚትሮች ርቀት ውስጥም የሰሜን ብሔራዊ ፓርክን በናሙናነት ነቅሰዋል።

አቶ ቻላቸው፤ በባሕር ማዶ ነዋሪ ኢትዮጵያውያንን በተመለከተ፤ በተለይም በሆቴል ግንባታዎችና አገልግሎቶች ላይ ተሳትፎ ለማድረግ ካሹ ተገቢ ድጋፎች እንደሚደረግላቸውና ቅድሚያም እንደሚሰጣቸው ጠቁመዋል።
የጎንደር አንዱ ውብ መስህብ የጥምቀት በዓል አከባበር እንደሆነም አንስተዋል።

በተለይም በዘንድሮው በዓለ ጥምቀት ተቀማጭነታቸው አዲስ አበባ የሆነ የውጭ አገር አምባሳደሮች እንዲገኙና ስለ ጎንደር ቱሪዝም ለየአገሮቻቸው እንዲያስተዋውቁ ለማድረግ ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ጋር በመተባበር ጥረቶችና ሂደቶች እየተደረጉ መሆኑን ገልጠዋል።





