አንኳሮች
- ማርሻል አርት እና ሴቶች
- ማርሻል አርት አካልን እና ጭንቅላትን የሚያንጽ አርት ነው
- ከኳታር የተገኙ ትርፋቶች
ኢትዮጵያ ጌታቸው የቀድሞ የኳታር በሄራው ቡድን የማርሻል አርት እና ቴኳንዶ አሰልጣኝ ስትሆን ወደዚህ ሙያ የተቀላቀለችው ገና የዘጠኝ አመት ታዳጊ በሆነችበት እድሜዋ ነበር ።

አጀማመሯም የተስተካከለ የአካል ብቃት ማሰልጠኛ በሌለበት በመውደቅ፤ በመነሳት ፤ በመሰበር እና በማገገም አሰልቺ እና አስቸጋሪ በሆነ የስልጠና ጊዜ ነበር ትላለች።

ዛሬ ሙያ አድርጋ የያዘችውን የማርሻል አርት እና ቴኳንዶ ከመሰረቱ ጀምሮ አሰልጥኖ ለዚህ ያበቃትም ሁሌም ከአፏ የማትለየው ማስተሯ እና ወንድሟ አየናቸው ጌታቸው ነበር ።
ኢትዮጵያ የባህር ማዶ ህይወቷን በዱባይ ብትጀምርም ሙያዋን በተግባር እንድታውል በሯን ከፍታ የተቀበለቻት አገር ግን ኳታር ነበርች። እንደ ኢትዮጵያ አባባልም የኳታር መንግስት ለስፓርት ከሚሰጠው ከፍተኛ ትኩረት እና እገዛ የተነሳ እሷም የአገሪቱን የብሄራዊ ቡድን በማርሻል አርት እና ቴኳንዶ ለማሰልጠን እድሉ አግኝታ ቡድኑን ከውጤት ጋር ለ11 አመታት ያህል አሰልጥናለች።

ኢትዮጵያ በአሁን ሰአትም ባለችበት ኳታር በግል አሰልጣኝ በመሆን እያገለገለች ትገኛለች።





