አንኳሮች
- የሐረር ከተማ አቆራቆር
- ጀጎል
- ሐረር የፍቅር፣ የመቻቻልና ሰላም ከተማነት
ሐረር
ሐረር ከኢትዮጵያ ጥንታዊና የስልጣኔ ማዕከል ከተሞች ውስጥ አንዷ ናት።
በአቶ ተወለዳ አብዶሽ - የሐረሪ ክልል የባሕል፣ ቅርስና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ፤ ስለ ሐረር ታሪካዊ መነሻት ሲናገሩ የሃርላ ሥርወ መንግሥት ያጣቅሳሉ፤ ከአክሱም ቀጥሎ የራሳቸው የመገበያያ ሳንቲም የነበራት፣ አሁንም ድረስ በሙዚየሟ ውስጥ ተጠብቀው ስለመኖራቸው፣ ጥንታዊ አሠፋፈርና የአኗኗር ዘዬዋን ይዛ መቆየቷን በዋቤነት በመንቀስ ዘመናት ያሸመገለ የዕድገት ደረጃዋን በማሳያነት ያመላክታሉ።

አክለውም፤ የሐረር ከተማ ከአዲስ አበባ ቀጥላ በጣም በርካታ የብሔረሰቦች፣ ሃይማኖቶችና ያለፉ ሥርዓተ መንግሥታትን ቅርሶች በሙዚየሟ አቅፋና ጠብቃ ያለች መሆኗን ያስረዳሉ።
የቱሪዝም መስህቦቿ በሙዚየም ስብስቦች ብቻ የተወሰኑ እንዳልሆኑና እስካሁንም የአያሌ የአገር ውስጥና የባሕር ማዶ ቱሪስቶችን ቀልብ ስቦ ዘልቆ ያለውን ጅብን የመቀለብ የምሽት ክንውን ያነሳሉ።

ሐረር እንኳን ሰው ጅቡም ከሰው ጋር ተባብሮ የሚኖርባት የሰላም፣ የመቻቻልና የፍቅር ከተማነቷ በ2003 ለሰላም ከተማ ስየማና ተሸላሚነት እንዳበቃትም ያወጋሉ።

የሐረር ከተማ ጥንታዊ የስልጣኔና አኗኗር አሻራ ማሳያ ከሆኑት ድንቅ ኪነ ሕንፃ ሥራዎች በዩኒስኮ የተመዘገበው ጀጎል ተጠቃሽ ሲሆን፤ የአለላ ጥበብ ሥራዎች፣ የመፅሐፍ ጥረዛና ባሕላዊ የዕደ ጥበብ ቅርሶችም ተነቃሽ ናቸው።

አቶ ተወለዳ አብዶሽ፤ የሐረሪ ክልል የባሕል፣ ቅርስና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ፤ በተለይም በአውስትራሊያ ለሚኖሩ የሐረሪ ተወላጆችና ኢትዮጵያውያን፣ በሌሎችም ከፍለ ዓለማት ለሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን የጉብኝት ጥሪያቸው ሲያቀርቡ "ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ሐረርን እንዲያውቋት፣ ሐረርን እንዲጎበኟት፣ ሐረር የኢትዮጵያ አንደኛዋ ገፅታና የስልጣኔ ማዕከል መሆኗን እንዲረዱና በተለይም፤ ከረመዳን ፆም ስድስተኛ ቀናት በኋላ በሚከበረው የሸዋሊድ በዓል እንዲገኙ ጥሪ አቀርባለሁ" ብለዋል።





