አባ በቀለ ዓይናለም አየለ ይባላሉ። የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ፕሮጄክት ዋና ሥራ አስኪያጅ የነበሩት ኢንጂነር ስመኘው አባት ናቸው። ልጃቸው ጁላይ 26, 2018 የራሳቸውን ሕይወት መስቀል አደባባይ ላይ በ53 ዓመታቸው እንዳጠፉ በፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን አማካይነት ተገልጧል።
አባ በቀለን ያገኘናቸው ዕድሜ፣ የጤና እጦት፣ ኃዘንና ጉስቁል ኑሮ ተጭኗቸው ነው።

SBS አማርኛ በወርኃ መስከረም ወደ ኢትዮጵያ ዘልቆ፤ ጎንደር አቅንቶ በነበረበት ወቅት ነበር ከጎንደር ስምንት ኪሎ ሜትር ፈንጠር ብላ ከምትገኘው ቀያቸው ሸምበቂት ደርሰን ያነጋገርናቸው።

መጠይቃችንን የጀመርነው “ከልጅዎ ሕልፈተ ሕይወት በኋላ ከኃዘንዎ እንደምን እየተጽናኑ፤ ኑሮዎን እንዴት እየገፉ ነው?” በሚል ነበር።
ኃዘኑ እንደጎዳቸው፤ ኑሮም እንደከበዳቸው ይናገራሉ። በጎንደር አስተዳደር በኩል የነጻ ሕክምና ቃል ቢገባልኝም ያገኘሁት ነጻ ሕክምና የለም ይላሉ።
ስለ ልጃቸው አሟሟት ሲያነሱ በመንግሥት በኩል እንደተገለጠው ራሱን በራሱ አጥፍቷል ብለው አያምኑም።

ጸጸታቸው “እኔን ሳይቀብረኝ፤ ልጆቹን ሳያሳድግ ሔደ” የሚል ነው።






