ሰሞኑን ከእዚህ ዓለም ለመጨረሻ ጊዜ ለተለዩት የማኅበረሰብ መሪ፣ ቅን አገልጋይ፣ የሶስት ልጆች አባትና መልካም ወዳጅ ዶ/ር ብርሃኑ ወልደኪዳንን ሕልፈተ ሕይወት አስመልክቶ ልጃቸው ሚካኤል ብርሃኑና የቅርብ ወዳጆቻቸው የተሰማቸውን ጥልቅ ሐዘን ይገልጣሉ። ለዶ/ር ብርሃኑ ቤተሰቦችና የማኅበረሰብ አባላት በሙሉ መፅናናትን ይመኛሉ።
ዶ/ር ብርሃኑ በጨለማ ብርሃን ሆነኝ። ትውውቃችን ለጥቂት ጊዜ ቢሆንም፤ በልቤ ውስጥ የነበረው ቦታ ግን ትልቅ ነው። ቤተሰብ ለመሆን ረጅም ዓመት አያስፈልግም። የሚያስፈልገው ንፁሕ ልብና ቅንነት ነው። ዶ/ር ብርሃኑም ያ ነበረው። እሱን በማወቄ ደስተኛ ነኝ። ብዙ ባለመቆየቱ ግን በጣም ሐዘንተኛ ነኝ። ማኅበረሰቡ ትልቅ ቅርስ ነው ያጣው።ሲስተር አሰገደች ብርሃኑ
ዶ/ር ብርሃኑን እንዲህ በቅርብ ጊዜ እናጣዋለን ብዬ አስቤ አላውቅም። የእሱ ሕይወት ማለፍ የቤተሰቡ ብቻ አይደለም። አንድ ትልቅ ዋርካ እንደወደቀ ነው የማየው። ጉድለቱ ለምናውቀው፤ ለምንቀርበው ብቻ ሳይሆን ለጠቅላላው ኢትዮጵያውያን ጉድለት ነው ብዬ ነው የማስበው። ብርሃኑ ሰው ሆኖ ነው ያለፈው። መልካም ስም ይዞ ነው ያለፈው። ፍፁም ኢትዮጵያዊ ነበር። እግዚአብሔር ለቤተሰቦቹ በሙሉ መፅናናትን እንዲሰጥ እጠይቃለሁ።የማኅበረሰብ አገልጋይ አቶ እሸቱ ሙሉጌታ
Share






