አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን የአቶ ተመስገን ጥሩነህን ቦታ በመተካት የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ሆነው ተሹመዋል።
አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን የዛሬው ሹመት እስኪሰጣቸው ድረስ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ብሔራዊ ደህንነት አማካሪ ሆነው እየሠሩ የነበረ ሲሆን ከኢሕአዴግ ጊዜ አንስቶ እስካሁን በስልጣን ላይ የሚገኙ ናቸው።
በሌላ በኩል ትዕግስት ሃሚድ ከኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ምክትል ዳይሬክተርነት ዋና ዳይሬክተር ሆነው በጠቅላይ ሚኒስትሩ ተሹመዋል።

አዲሶቹ ተሿሚ ሚኒስትሮች እነማን ናቸው?
6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 3ኛ ዓመት የስራ ዘመን በ15ኛ መደበኛ ስብሰባው የአቶ ተመስገን ጥሩነህን ፣ አምባሳደር ታዬ አፅቀሥላሴንና የዶ/ር መቅደስ ዳባን ሹመት አጽድቋል፡፡
በጠ/ሚኒስትሩ አቅራቢነት ምክር ቤቱ በሙሉ ድምጽ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እንዲሆኑ ሹመታቸውን ያፀደቀላቸው አቶ ተመስገን ጥሩነህ ሲሆኑ በጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት አቶ ቴዎድሮስ ምህረት እየተመሩ ቃለ መሃላ ፈጽመዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ የቅርብ ሰው እንደሆኑ የሚነገርላቸው አቶ ተመስገን ፤ ሻለቅነት ማዕረግ በደረሱበት የመከላከያ ሰራዊት ውስጥ፤ በመረጃ ዋና መምሪያ፣ ኤሌክትሮኒክስ መምሪያ እና ቴክኒካል መረጃ መምሪያ ስር አገልግለዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ወደ ስልጣን ከመጡ በኋላ በሚያዝያ 2010 ዓ.ም. ፤ ኢንሳን በዋና ዳይሬክተርነት እንዲመሩ አቶ ተመስገንን ሾመዋቸው የነበረ ሲሆንሲሆን ፤ በጥቅምት 2011 ዓ.ም. አብይ ለተለያዩ የመንግስት ኃላፊዎች ሹመት ሲሰጡ፤ አቶ ተመስገን በሚኒስትር ማዕረግ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የብሔራዊ ደህንነት ጉዳዮች አማካሪነት ቦታን አግኝተዋል።

በመቀጠልም የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር የነበሩት ዶ/ር አምባቸው መኮንን እና ሌሎች ሁለት ከፍተኛ አመራሮች በሰኔ 2011 ዓ.ም. መገደላቸውን ተከትሎ፤ አቶ ተመስገን ክልሉን የመምራት ኃላፊነትን ተረክበዋል።
በአማራ ክልል፣ ምስራቅ ጎጃም ዞን ብቸና፣ ልዩ ስሙ ወይራ በተሰኘ አካባቢ የተወለዱት አቶ ተመስገን፤ በጥቅምት 2013 ዓ.ም. በትግራይ ክልል ጦርነት ሲቀሰቀስ ከክልል መሪነታቸው ተነስተው፤ የፌደራሉን የብሔራዊ መረጃ እና ደህንነት አገልግሎት በዋና ዳይሬክተርነት እንዲመሩ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ተሹመው በዚሁ የኃላፊነትም ቆይተዋል።
ሁለተኛው ተሿሚ አምባሳደር ታዬ አፅቀሥላሴ ሲሆኑ እርሳቸውም የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር ሆነው በፓርላማው ፊት ቃለ መሐላ ፈፅመዋል።
አቶ ታዬ የተመድ ቋሚ መልዕክተኛ ሆነው ከመስከረም 2011 ዓም አንስቶ እስከ ጥር 2015 ዓም ድረስ ማገልገላቸው ይታወሳል።

አምባሳደሩ ወደ ተመድ ኃላፊነትም ከመምጣታቸው አስቀድሞ በግብፅ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሆነው አገልግለዋል።
በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ውስጥም ሚኒስትር ዴኤታን ጨምሮ በሌሎች ከፍተኛ ኃላፊነቶች የሰሩት አዲሱ ተሿሚ በአሜሪካ ዋሽንግተን የኢትዮጵያ ኤምባሲ አማካሪ እና በሎስአንጀለስ የኢትዮጵያ ዋና ቆንስላ በመሆንም ለረጅም ዓመታት በኃላፊነት ያገለገሉ ሲሆን ወደዚህ ኃላፊነት የመጡት አቶ ደመቀ መኮንን በመተካት ነው።
አምባሳደር ታዬ የመጀመሪያ ዲግሪ በፖለቲካ ሳይንስና አለም ዓቀፍ ግንኙነት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ያገኙ ሲሆን ሁለተኛ ዲግሪያቸውን ደግሞ ከእንግሊዝ ላንካስተር ዩኒቨርሲቲ በዓለምቀፍ ግንኙነትና ስትራቲጂያዊ ጥናት አግኝተዋል።
በዕለቱ ሹመት ከተሰጣቸው አንዷና ብቸኛዋ ሴት የሆኑት ደግሞ ዶክተር መቅደስ ዳባ ሲሆኑ የጤና ሚኒስቴር ሚኒስትርነትን ኃላፊነት ተረክበዋል።
በአዲስ አበባ ከተማ የተወለዱት ዶክተር መቅደስ ዳባ የሕክምና ድግሪያቸውን ከሀዋሳ ዩኒቨርስቲ ያገኙ ሲሆን ሲሆን፤ ከቅዱስ ጳውሎስ ሚሊኒየም ሜዲካል ኮሌጅ በቤተሰብ ዕቅድ የድህረ ምረቃ ትምህርታቸውን ተከታትለው ከፍተኛ የማህፀን እና የጽንስ ሐኪም እና የኅብረተሰብ ጤና ስፔሻሊስት ሆነዋል።

በተጨማሪም የኢትዮጵያ የጽንስ እና ማህጸን ማኅበር ፕሬዚዳንት፤ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የማህጸን እና ጽንስ ትምህርት ክፍል መምህር በመሆን ያገለገሉት አዲሷ ተሿሚ ፤ ዓለም አቀፍ የመራቢያ አካላት ጤና ማሰልጠኛ ማዕከል (CIRHT) አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር፣ በኢትዮጵያ የተመድ ሴቶች ሲቪል ማህበረሰብ አማካሪ ቡድን አባል በመሆንም ሰርተዋል።
ጄኔቫ በሚገኘው በዓለም ጤና ድርጅት የምክትል ዳይሬክተሩ ልዩ ረዳት እና ከፍተኛ ባለሞያም ሆነው ያገለገሉት ዶ/ር መቅደስ በኢትዮጵያ የመጀመሪያዋ ሴት የቤተሰብ እቅድ እና የመራቢያ አካላት ጤና ንዑስ ስፔሻሊስትም ናቸው፡፡
በተጨማሪም ፤ በማኅጸን እና ጽንስ ህክምና ዘርፍ ባደረጉት ምርምር እና አስተዋጽዖ በሴቶች ዘርፍ እ.አ.አ የ2021 የዓለም የጽንስ እና ማኅፀን ህክምና ሽልማትን አሸንፈዋል።
ዶክተር መቅደስ ዳባ ባለትዳር እና የሁለት ልጆች እናት መሆናቸውን ከግለ ታሪካቸው የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡
አዲሷ ተሿሚ ወደዚህ ኃላፊነት የመጡት ከመጋቢት 2012 ዓ.ም አንስቶ በሚኒስትርነት ሲያገለግሉ የቆዩትን ዶ/ር ሊያ ታደሰን ተክተው ነው።

