የአክሱም ሀውልት ዳግም ለጎብኚዎች ክፍት መደረጉን በትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር የአክሱም ከተማ ባህልና ቱሪዝም ጽሕፈት ቤት አስታወቀ።
የጽሕፈት ቤቱ ሀላፊ አቶ ገብረመድህን ፍፁም ብርሀን ለኢዜአ እንዳስታወቁት፤ በአክሱም ከተማና አካባቢው የሚገኙ የሚዳሰሱ እና የማይዳሰሱ ጥንታዊ ቅርሶች ለቱሪስቶች ክፍት ተደርገዋል።
ቅርሶቹ ዳግም ለጎብኚዎች ክፍት እንዲሆኑ ሕብረተሰቡ በጉልበቱ፣ በገንዘቡና በሙያው ያደረገው ተሳትፎ የላቀ እንደነበርም ተናግረዋል።
የቱሪዝሙን ዘርፍ ወደነበረበት ለመመለስና ሕብረተሰቡ ለቱሪስቶች የሚሰጠውን አገልግሎት ለማሳደግ ለፎቶ ግራፍ ባለሙያዎች፣ አስተርጓሚዎች፣ ለባህላዊ ጌጣጌጦችና ቅርፃቅርፅ ባለሙያዎች እንዲሁም ለባለ ሆቴሎች ስልጠና መሰጠቱን አስረድተዋል።
በአክሱምና አካባቢው የሚገኙ ቅርሶችና ሙዚየም ለጎብኚዎች ተደራሽ ለማድረግ ከዛሬ ጀምሮ ክፍት መደረጋቸውን ገልጸዋል።
በአክሱምና አካባቢው የሚገኙ የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ ጥንታዊ ቅርሶች ለመጎብኘትና ለማየት በየአመቱ ከ30 ሺህ በላይ የውጭ ሃገር ቱሪስቶች ይጎበኙት እንደነበር አስታውሰዋል።
ጎብኝዎቹ በአክሱምና አካባቢ በሚኖራቸው ከ2 እስከ 3 ቀናት ቆይታ ከሚያገኙት አገልግሎት የቱሪዝም ጽህፈት ቤቱና ነዋሪው በዓመት ከ180 ሚልዮን ብር በላይ ገቢ ያገኝ እንደነበረም ጠቅሰዋል።