መምህርና ደራሲ ምንተስኖት መንገሻ ነዋሪነታቸው ሎንዶን - አገረ እንግሊዝ ነው። በኒው ሲቲ ኮሌጅ የማስተማር ዘዴ መምህር ናቸው። በሃብት ቁመናዋ ከመጀመሪያው ረድፍ ላይ በምትሰለፈዋ አገረ እንግሊዝ ጣቶቻቸው ከተበጫጨቀ ጫማዎቻቸው ሾልከው ለወጡ ተማሪ ሕፃናት መርጃ የሚውል ገንዘብ እንደምን በባዶ እግራቸው ተጉዘው እንዳሰባሰቡ ይናገራሉ። ለአገራቸው ለኢትዮጵያ ተረጂዎችም በላየንስ ክለብ በኩል እርዳታ አሰባስበዋል፤ የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል የዕድሜ ልክ አባልም ናቸው።
አንኳሮች
- የበጎ አድራጎት ተግባርና ሽልማት
- ድህነትና ሕፃናት በአገረ እንግሊዝ
- የቀድሞ ግብረ ሰናይ ተግባራትና የወደፊት የረድኤት ውጥኖች
አትሳቅ አትበሉኝ
ጭጋግ መሬት ቢረግጥ
ጸሃይ ብትሸፈን፣
አየሩ ቢታፈን፣
ኑሮ ረመጥ ቢሆን፣
ዙሪያው ገባው ሁሉ
ማቅ ለብሶ ቢዳፈን፡፡
ሳቄን ማን ከልክሎኝ፣
አልፎ ሂያጂነቴን
ጉዞዬን ማን ገቶኝ፣
እርቃኔንም ብሆን
የውስጤን ነጻነት እንደያዝኩት አለሁ
በውስጤ ሃብት አለኝ፡፡
አትሳቅ አትበሉኝ ... ሳቄ የቀረ ዕለት፣
የደኸየሁ እንደሁ ... በፈገግታ ንፍገት፣
ያኔ ነው የኔ ሞት፡፡
ጫማም አላቂ ነው
ከስር ተሸንቁሮ፣
ልብስም ይቀደዳል
ውሉ ተተርትሮ፣
ሁሉም አላፊ ነው
ያረጃል ያፈጃል
ትናንትም አርጅቶ
ጥንት ይባላል ዱሮ፡፡
አትሳቅ አትበሉኝ ... ሳቄ የቀረ ዕለት
የደኸየሁ አንደሁ ... በፈገግታ ንፍገት፣
ያኔ ነው የኔ ሞት፡፡
.............................
መታሰቢያነቱ ለጫማ አልባው ብላቴና ይሁንልኝ ... ጸደይ 2020
ምንተስኖት መንገሻ






