ዳባሳ ዋቅጅራ፤ ከዘመቻ ወደ ስደት

Community

Dabassa Waqjira. Source: D.Waqjira

የ1998 / 1990ው የኢትዮ - ኤርትራ ጦርነት አቶ ዳባሳን ለጦር ግንባር ሪፖርተርነት ብቻ አብቅቶ አልተወሰነም። ከቶውንም በወቅቱ ከኤርትራ መንግሥት ጋር ተመሳጥሮ በኢትዮጵያ ላይ የጥቃት እጁን ቃጥቷል ተብሎ በተፈረጀው የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) ወገንተኝነት ተጠርጣሪ አድርጓቸዋል። የጥርጣሬው ክስም "የኦነግ መንፈስ አለበት። የኢትዮጵያ መንግሥት ከሻዕቢያ ጋር የሚያደርገውን ጦርነት አይደግፍም። ለሻዕቢያ ያደላል" የሚል ሲሆን፤ የእሳቸው ምላሽ ግና "የለም ሙያዬና ኦነግ አይገናኙም" ነበር።


አቶ ዳባሳ ከአንድ ወር የግንባር ቆይታና ግምገማ በኋላ ወደ አዲስ አበባ እንዲመለሱ ተወሰነ።

አዲስ አበባም ተመልሰው መደበኛ ሥራቸውን ማከናወን ጀመሩ።
Community
Dabassa Waqjira. Source: D.Waqjira
ክትትሉ ቀጠለ።

የድንበር ጦርነቱ አበቃ።  

በምትኩ የአገር ውስጥ ተቃውሞ በኦሮሚያና አዲስ አበባ ተቀጣጠለ። 

ያም ሪፖርትህ "የተዛባ ነው" የሚል ግምገማ አስከተለ።

የመንግሥት ትዕግሥት አለቀ።

ዓርብ ኤፕሪል 30 - 2004 አቶ ዳባሳ በፀጥታ ኃይሎች ከቢሮአቸው ታግተው ዘብጥያ ወረዱ።

"ለኦነግ መረጃ ታቀብላለህ" የሚል ክስ ተመሠረተባቸው። 

ክሳቸው ሲመረመርና ፍርድ ቤት ሲቀርብ ቆይቶ ከሶስት ዓመታት እሥር በኋላ በፍርድ ቤት ትዕዛዝ በነፃ ተለቀቁ። 

ወደ ኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ሔደው የቀድሞ ሥራቸው ላይ እንዲመለሱ ጠየቁ።

ጥያቄያቸው ውድቅ ሆነ። ይልቁንም ክትትሉ ቀጠለ።

ሁኔታውን አውጥተው አውርደው ከሥር ከተፈቱ ከአንድ ወር በኋላ ድንበር አቋርጠው ኬንያ ዘለቁ።

ጥገኝነት ጠየቁ።

ጥገኝነት ጥየቃና የስደተኛነት ዕውቅና

አቶ ዳባሳ ኬንያ ገብተው ጥገኝነት በጠየቁ አጭር ጊዜያት ውስጥ የስደተኛነት ዕውቅናን ከተባበሩት መንግሥታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን አገኙ።

ወደ ስደተኞች ካምፕ እንዲያመሩ ተነገራቸው።

ወደ ስደተኞች ካምፕ ከሔዱ ሕይወታቸው ይበልጡኑ ለአደጋ እንደሚጋለጥ በማመላከት ለኮሚሽኑ አቤት አሉ።

ኮሚሽኑም ይሁንታውን ቸራቸው።
Community
Dabassa Waqjira. Source: D.Waqjira
የስደት ኑሮአቸውን ናይሮቢ ውስጥ መግፋት ጀመሩ።     

እንዲያ እያሉ እንደሳቸው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የኦሮምኛ ዝግጅት ክፍል ጋዜጠኛ የነበሩት ባለቤታቸው ከሶስት ልጆቻቸው ተነጥለው ለእሥር ተዳረጉ።

በአቶ ዳባሳ ላይ ከፍተኛ የመንፈስ ጭንቀት አደረ። 

ወደ አገር ቤት በመመለስና በስደት በመቆየት መካከል ዋለሉ።

ከባለቤታቸው የሶስት ወራት እሥራት በኋላ በዘመድ አዝማድ እገዛ ልጆቻቸውን ወደ ኬንያ አስመጡ።

አባትና ልጆች በስደተኛነት ተመዝግበው የሚያሰፍራቸውን አገር ሰብዓዊ ትድግና መጠባበቅ ጀመሩ።

አውስትራሊያ እጇን ዘረጋች።

ከልጆቻቸው ጋር እ.አ.አ ሴፕቴምበር 2009 አደላይድ ደቡብ አውስትራሊያ ዘለቁ።   

 

 


Share
Follow SBS Amharic

Download our apps
SBS Audio
SBS On Demand

Listen to our podcasts
Independent news and stories connecting you to life in Australia and Amharic-speaking Australians.
Ease into the English language and Australian culture. We make learning English convenient, fun and practical.
Get the latest with our exclusive in-language podcasts on your favourite podcast apps.

Watch on SBS
SBS World News

SBS World News

Take a global view with Australia's most comprehensive world news service