አቶ ዳባሳ ከአንድ ወር የግንባር ቆይታና ግምገማ በኋላ ወደ አዲስ አበባ እንዲመለሱ ተወሰነ።
አዲስ አበባም ተመልሰው መደበኛ ሥራቸውን ማከናወን ጀመሩ።
ክትትሉ ቀጠለ።

Dabassa Waqjira. Source: D.Waqjira
የድንበር ጦርነቱ አበቃ።
በምትኩ የአገር ውስጥ ተቃውሞ በኦሮሚያና አዲስ አበባ ተቀጣጠለ።
ያም ሪፖርትህ "የተዛባ ነው" የሚል ግምገማ አስከተለ።
የመንግሥት ትዕግሥት አለቀ።
ዓርብ ኤፕሪል 30 - 2004 አቶ ዳባሳ በፀጥታ ኃይሎች ከቢሮአቸው ታግተው ዘብጥያ ወረዱ።
"ለኦነግ መረጃ ታቀብላለህ" የሚል ክስ ተመሠረተባቸው።
ክሳቸው ሲመረመርና ፍርድ ቤት ሲቀርብ ቆይቶ ከሶስት ዓመታት እሥር በኋላ በፍርድ ቤት ትዕዛዝ በነፃ ተለቀቁ።
ወደ ኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ሔደው የቀድሞ ሥራቸው ላይ እንዲመለሱ ጠየቁ።
ጥያቄያቸው ውድቅ ሆነ። ይልቁንም ክትትሉ ቀጠለ።
ሁኔታውን አውጥተው አውርደው ከሥር ከተፈቱ ከአንድ ወር በኋላ ድንበር አቋርጠው ኬንያ ዘለቁ።
ጥገኝነት ጠየቁ።
ጥገኝነት ጥየቃና የስደተኛነት ዕውቅና
አቶ ዳባሳ ኬንያ ገብተው ጥገኝነት በጠየቁ አጭር ጊዜያት ውስጥ የስደተኛነት ዕውቅናን ከተባበሩት መንግሥታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን አገኙ።
ወደ ስደተኞች ካምፕ እንዲያመሩ ተነገራቸው።
ወደ ስደተኞች ካምፕ ከሔዱ ሕይወታቸው ይበልጡኑ ለአደጋ እንደሚጋለጥ በማመላከት ለኮሚሽኑ አቤት አሉ።
ኮሚሽኑም ይሁንታውን ቸራቸው።
የስደት ኑሮአቸውን ናይሮቢ ውስጥ መግፋት ጀመሩ።

Dabassa Waqjira. Source: D.Waqjira
እንዲያ እያሉ እንደሳቸው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የኦሮምኛ ዝግጅት ክፍል ጋዜጠኛ የነበሩት ባለቤታቸው ከሶስት ልጆቻቸው ተነጥለው ለእሥር ተዳረጉ።
በአቶ ዳባሳ ላይ ከፍተኛ የመንፈስ ጭንቀት አደረ።
ወደ አገር ቤት በመመለስና በስደት በመቆየት መካከል ዋለሉ።
ከባለቤታቸው የሶስት ወራት እሥራት በኋላ በዘመድ አዝማድ እገዛ ልጆቻቸውን ወደ ኬንያ አስመጡ።
አባትና ልጆች በስደተኛነት ተመዝግበው የሚያሰፍራቸውን አገር ሰብዓዊ ትድግና መጠባበቅ ጀመሩ።
አውስትራሊያ እጇን ዘረጋች።
ከልጆቻቸው ጋር እ.አ.አ ሴፕቴምበር 2009 አደላይድ ደቡብ አውስትራሊያ ዘለቁ።