አንኳሮች
- በሺህዎች የሚቆጠሩ ሕፃናት በኃይል ከቤተሰቦቻቸው ተነጥቀው ወደ ነጩ ሕብረተሰብ ተወሰዱ።
- ነጠቃዎቹም ከትውልድ ወደ ትውልድ ተሻጋሪ ጥልቅ የስሜት ሁከትን አስከትሎ ዘለቀ።
- ዛሬ ማኅበረሰባቱ በባሕላዊ ዳግም ቁርኝትና የድጋፍ ፕሮግራሞች አማካይነት በፈውስ ሂደት ላይ ናቸው።
- የፈውሱ ቁልፍም ትምህርትና ብሔራዊ ዕርቅ ናቸው።
የይዘት ማስጠንቀቂያ፤ ይህ ክፍለ ዝግጅት የውስጣዊ ስሜት ሁከትንና የሕፃናት ነጠቃን ያካተቱ አስጨናቂ፣ እንዲሁም፤ በሕይወት የሌሉ የአቦሪጅናልና ቶረስ መሽመጥ ደሴት ነዋሪዎችን ጠቃሽ ይዘቶችን አካትቶ ይዟል።
ከ1910 እስከ 1970 ዓ.ም. ድረስ፣ በሺህዎች የሚቆጠሩ የአቦርጂናልና ቶረስ መሽመጥ ደሴት ልጆች በይፋ የመንግሥት ፖሊሲ መሠረት ከቤታቸው ተነጥቀው ተወሰዱ። እኒያም ልጆች ለተቋማት ተሰጡ ወይም ነባር ዜጎች ያልሆኑ ቤተሰቦች ማደጎዎች ሆኑ።
ልጆቹ ተነጥቀው የተወሰዱት ስለምን ነበር?
የብሩም ቀዬ የያውሩ ማኅበረሰብ አባል እና የፈውስ ፋውንዴሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ የሆኑት ሻናን ዶድሰን ሲገልጡ፣ ከነጠቃው ጀርባ አጥፊ የሆነ ዓላማ እንደነበር ያስረዳሉ።
"የተሰረቁት ትውልዶች ልብ ሰባሪው ነገር፤ በአሥር ሺህዎች የሚቆጠሩ ሕፃናት ከቤተሰባቸው መለየታቸው ነው። ዋነኛ አስባቡም ነባር ዜጎች ካልሆኑ ቤተሰቦች ጋር ማንነታቸውን ረስተው እንዲኖሩ ለማድረግ ነው። ብዙዎቹ ለግፍና አሰቃቂ ሁኔታዎች ተዳርገዋል፤ አብዛኞቹም ቤተሰቦቻቸውን ደግመው አላዩም" ሲሉ።
ሕፃናት በተለይ ዒላማ የሆኑበት ምክንያትም በአብዛኛው የተነገራቸውን ስለሚቀበሉና ባሕላቸውንም አሌ ስለሚሉ ነው። ቤተሰቦች ተዘውትሮ ልጆቻቸው እንደሞቱ ወይም እነሱን እንደማይፈልጓቸው ተደርጎ እውነት ያልሆነ ነገር ይነገራቸው ነበር።
በአግባቡ የተያዘ ሬኮርድ ባለመኖሩም በትክክል ምን ያሕል ሕፃናት ተነጥቀው እንደተወሰዱ ለማወቅ አዋኪ ነው፤ ይሁንና ቁጥሩ ከሶስት ሕፃናት አንድ ያህል ከፍ ያለ ይሆናል። ይሁንና፤ እያንዳንዳቸው የአቦርጂናልና ቶረስ መሽመጥ ደሴት ማኅበረሰብ አባላት ከነ አካቴው መቀየራቸውንና ጠባሳውም አብሯቸው እንዳለ እናውቃለን።

ልጆቹ ወደ የት ተወሰዱ?
አያሌ ሕፃናት በመላ ሃገሪቱ ወደ ክፍለ ሃገራትና ቤተክርስቲያን መራሽ ተቋማት ተወስደዋል።
እኒያም ሕፃናቱን በእጅጉ ጥብቅ ለሆነ ሥርዓት ማስያዣ ማሰልጠኛ ማዕከላት ወይም ማደሪያዎች ተደርገው ይጠቀሱ ነበር። ማንነታቸውን ተነጥቀው አዳዲስ ስሞች፣ ቋንቋና ሃይማኖት ተሰጥቷቸዋል።
በአብዛኛው ዘመዳሞች እንዲለያዩ ተደርገዋል፤ ጥቂት ተቋማት ይቀበሉ የነበሩት ጨቅላ ሕፃናትን ብቻ ነበር።
በ1943 የአራት ዓመቷ ሕፃን አክስት ሎሬየን ፒተርስ፤ የጋሚላሮይና ዋይልማን ሴት ኒው ሳውዝ ዌይልስ ወደሚገኘው ኮታማንድራ ለነባር ዜጎች የቤት ውስጥ ሠራተኛ ማሰልጠኛ ተወስደዋል። ሁለቱ ወንድሞቻቸው በአስከፊነቱ ወደሚታወቀው ኪንቼላ የነባር ዜጎች ማሰልጠኛ ተልከዋል።
“ነጭ መሆንህን ከረሳህ ቅጣቱ ቅፅበታዊ ነው፣”
“የነባር ዜጎች ሰዎች ስለመሆናችን ከቶውንም አናነሳም። ገና በአራት ዓመቴ ማንነቴን እንድረሳ ተደረግሁ። ብዙም ሳይቆይ የነባር ዜጎች አኗኗርን ዘንግተህ የነጭ አኗኗርን ትማራለህ። በእነዚያ ሥፍራዎች ቅጣቱ አሰቃቂ ነበር” ሲሉ ገልጠዋል።
አክስት ሎሬይን ለቀጣዮቹ 10 ዓመታት ለነጭ ቤተሰቦች በቤት ሠራተኛነት እንዲሰለጥኑ ተደረገ።
ዛሬ በእዚያ ሕይወት ውስጥ አልፈው ለተረፉት ብርቱ ድምፅ ሆነው አሉ፤ ተገድደው ለተወሰዱቱ በልክ የተነደፈ የፈውስ ተነሳሽነት ያለው የማሩማሊ ፕሮግራም መሥራች ሆነው አሉ።

ትውልድ ተሻጋሪ የመንፈስ ሁከት ምንድን ነው?
ልጆች፣ ቤተሰቦችና ማኅበረሰባት ያለፉባቸው የመንፈስ ሁከት ከትውልድ ወደ ትውልድ ይተላልፋል።
አክስት ሎሬይን፤ በአሁኑ ወቅት ማን እንደሆኑ፣ ከየት እንደመጡና ስለምን የተለየ ባሕሪይ እንዳላቸው የማያውቁና የማንነታቸው ውል የጠፋባቸው እንዳሉ ይናገራሉ። ።
“የክቦሽ አዙሪት ዑደት ነው። በቤተሰባችን ውስጥ ልንሰብረው ካልቻልን፤ ዑደቱ ይቀጥላል” ይላሉ።
ከታሪካዊ የድጋፍ ሥርዓት እጦት ሳቢያ፤ የአያቶቻቸውና ወላጆቻቸው ስቃይ በቅርበት ከመመልከት በመነሳት የመንፈስ ሁከት ልብ ሳይሉት ወደ ልጆች ያልፋል።
ይህም ትውልድ ተሻጋሪ የመንፈስ ሁከት በመባል ይታወቃል።
ሰለባዎች ፍቅር ወይም አለሁ ባይነት በተመላበት ሁኔታ ባለማደጋቸው ሳቢያ፤ የራሳቸውን ልጆች ያለ ሁከት ለማሳደግ ምን ያህል አዋኪ እንደሁ እንደሚናገሩ ሻናን ዶድሰን ያስረዳሉ።
“የተወሰኑ ሰለባዎች ቀደም ሲል ባለፉበት የመንፈስ ሁከት ሳቢያ ሐዘን በታከለበት ስሜት የራሳቸውን የመንፈስ ሁከት ወደ ራሳቸው ልጆች እንዳሳለፉ ያምናሉ። እናም ዑደቱ ከልጅ ልጆች ወደ የልጅ ልጅ ልጆች ሲደጋገም እንመለከታለን። ለእዚያም ነው ትውልድ ተሻጋሪ ብለን የምናመላክተው” ሲሉ።
የትውልድ ተሻጋሪ የመንፈስ ሁከት ምልክቶች ዛሬ ከፍተኛ በሆነ የቤተስብ መፍረስ፣ አመፅ፣ እሥር፣ ራስን በራስ ማጥፋትና በአልኮል ሱስ መጠመድ በከፍተኛ ደረጃ ጎልተው ይታያሉ።
ማኅበረሰባት በአሁኑ ወቅት የመንፈስ ሁከት ዑደትን ለፍፃሜ ለማብቃት እየሠሩ ይገኛሉ።

ከመንፈስ ሁከት መፈወስ ምን ይመስላል?
ሻናን ዶድሰን “እንደማስበው ከሆነ ፈውስ ከሰዎች ሰዎች ይለያያል፤ ሆኖም ሰለባዎች ያ ፈውስ ምን ሊሆን እንደሚገባ ራሳቸው ለራሳቸው መወሰንን ግድ እንደሚል እናውቃለን” ይላሉ።
ፈውስ ማለት ቤተሰባዊ መዋቅሮችንና ብርቱ ማኅበረሰባትን መልሶ መገንባት ነው። እንዲሁም፤ የማንነትና የኩራት መንፈስን መልሶ መገንባት ማለትም ጭምር ነው። ከምድር፣ ባሕልና ቋንቋ ጋር መልሶ መዋደድ የተገፈፈ ማንነትን መልሶ ለመላበስ ይረዳል።
ሰለባዎች ያለፉበትን የሕይወት ተሞክሮዎች ሊያጋሩና ታሪካዊ ስለሆኑ ኢፍትሐዊነት በግልፅ ሊናገሩ ይገባል።
“በቅርርቦሽና አብሮ በመሰባሰብ ፈውስን እዚያው መፍጠር ይቻላል” የሚሉት አክስት ሎሬይን፤ በቀድሞ ኩታማንድራ ነዋሪዎች ከተመሠረተው የኩታ ነባር ዜጎች ልጃገረዶች ኮርፖሬሽን ጋር ስላላቸው ሥራ ያነሳሉ።
“አንስተው ያወጋሉ፣ ታሪኮቻቸውን በማውጋትና በማጋራትም ተፈውሰውበታል … አዘውትረው ያንን ሲያደርጉም የሚዘነጉ አይሆኑም" ሲሉ።
Intergenerational Trauma Animation, The Healing Foundation
This video contains the voice of a deceased person.
ትምህርትና እውነት ነገራ
ሌላው ሁነኛ የፈውስ ንጥረ ነገር ትምህርት ነው — መላ አውስትራሊያውያን የተሰረቁት ትውልዶችን እውነት መረዳት ሲችሉ።
አክስት ሎሬይን “ስለ እዚህች አገር [ነባር ዜጎች ያልሆኑ አውስትራሊያውያን] ለልጆቻቸው የእዚህችን ሀገር እውነተኛ ታሪክ እንዲማሩ ዕድል ሲሰጡ ማየትን እውዳለሁ”
“እንዲሁም፤ ሥርዓቶቹ ከስር ተነቅለው ሲጠፉ፣ ተመንግለው ተጥለው በምትካቸው በአዲስ ሁኔታ ሲጀመር። ስለምን ስለ እኛ ሰዎች የተፃፉት ዘረኛነት የተመላበት፣ ዘረኛነትን መሠረት አድርገው የተፃፉ ፖሊስዎች ናቸውና” ብለዋል።

ከተሰረቁት ትውልዶች ለተረፉቱ አሁን ያለው ምንድን ነው?
በ2008 ታሪካዊ ሁነት የወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ኬቨን ራድ ለረጅም ጊዜያት ሲጠበቅ የቆየ ይቅርታን ለተሰረቁት ትውልዶች፣ ዝርያዎቻቸውና ቤተሰቦቻችቸው ይቅርታን ጠይቀዋል።
ያን ተከትሎም የፈውስ ፋውንዴሽንን አካትቶ በርካታ ተነሳሽነቶችና አልሚ እንቅስቃሴዎች ተመሠረቱ።
ለሰለባዎችና ቤተሰቦቻቸው የሚያሿቸው ድጋፎች ስለመቀጠላቸውም ሻናን ዶድሰን ሲያመላክቱ፤
“የእኛ ድርጅት ለብሔራዊ ፈውስ ጥቅል ጎትጓች ነው፤ በአሳዛኝ ሁኔታ ተጨማሪ ሰለባዎች ከማለፋቸው በፊት ለተሰረቁት ትውልዶች ቀሪ ፍትሕ እንዲገኝ” ብለዋል።
ከፈውስ ፋውንዴሽንና ማኅበረሰብ መር ተነሳሽነቶች በሚገኝ ድጋፍ እንደ ማሩማሊ ያሉ ፕሮግራሞች የትውልድ ተሻጋሪ ፈውስ ሊቀጥል ይችላል።
እውነተኛ ፈውስ ስለ ሰለባዎች የታሪክ ግንዛቤን መጨበጥና በመላ አውስትራሊያም መደመጥን ግድ ይላል።
READ MORE

What is Closing the Gap?
ስለ አዲሱ የአውስትራሊያ ሕይወትዎ ተጨማሪ ጠቃሚ መረጃና ፍንጮች ለማግኘት የአውስትራሊያ ስትገለጥ ፖድካስትን ይከተሉ አሊያም ደንበኛ ይሁኑ።
ጥያቄዎች ወይም ርዕሰ ሃሳቦች ካለዎት? australiaexplained@sbs.com.au ኢሜይል ይላኩልን።







