ማኅበሩ ቀጣይ እንዲሆን መተባበር ያስፈልጋል። የኅብረተሰቡን ፍላጎት ማወቅ፣ የእምነት ቤቶችን፣ ወጣቶችንና ዕድሮችን ያማከለ፤ የተለያዩ አማራጭ ሃሳቦችን ሊያቀርብ የሚችል አንድ የተውጣጣ ቡድን ማቋቋም አስፈላጊ ይመስለኛል።ደራሲ አዳሙ ተፈራ፤ የቀድሞው በቪክቶሪያ የኢትዮጵያውያን ማኅበረሰብ ማኅበር ፕሬዚደንት፣
አሁን ያለውን ቦርድና ሥራ አስፈፃሚ ያማከለ ሆኖ፤ ልምድ ያላቸው የቀድሞ አመራሮችን፤ አስፈላጊ ከሆነ ተፅዕኖ አሳዳሪ ሰዎች ተጨምረው የማሻሻያ ለውጥ ቢደረግ፤ አሁን ባለው አመራር ላይ ሌላ ዓይነት ችግር እንዳይፈጠር ይረዳል።ዶ/ር ቢቾክ ዋን፤ በቪክቶሪያ ዩኒቨርሲቲ የማኅበራዊ ሳይንስ መምህር
አሁን ያለው ፍጥጫ አቅጣጫ ከሳተ ጥሩ አይሆንም፤ ወደ መበታተን ውስጥ እንገባና እንደገና ተቧድኖ ፍትጊያ ውስጥ ይገባል። ስለዚህ ሕገ ደንቡን አይቶ፤ በሥራ አሥፈፃሚውና ቦርዱ መካከል ያሉትን አለመግባባቶች የሚፈታ ጠንካራ የሚያቀራርብ ጊዜያዊ ኮሚቴ ቢቋቋም።አቶ ዓለማየሁ በዛብህ፤ የቀድሞው በቪክቶሪያ የኢትዮጵያውያን ማኅበረሰብ ማኅበር ዋና ፀሐፊ
አንዱ ማኅበረሰቡን ለማሰባሰብ የሚረዳን ስፖርት ነው። ሕዝቡን የሚያነቃቃ መንገድ ቢፈጠር ጥሩ ነው። ወጣቶቻችንን ከመጥፎ ነገር ለመጠበቅ ይረዳናል። አጥኚ ኮሚቴ በማቋቋም መፍትሔ ቢፈለግ እላለሁ።አቶ አሕመድ ዳውድ፤ የቀድሞው በቪክቶሪያ የኢትዮጵያውያን ማኅበረሰብ ማኅበር ቦርድና ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል (ዕገዳ ላይ)
አስቸኳይ ለሆነ ነገር በዙም መሰብሰብ ችግር የለውም፤ ነገር ግን ጠቅላላ የሕዝብ ስብሰባ በአዳራሽ እንዲሆን። መፍትሔ እንዲገኝ የሥራ አስፈፃሚና የቦድ አባላቱን ሰብስቦ የሚያወያይና ለጠቅላላ ጉባኤ የሚያቀርብ ልምድ ያለው ኮሚቴ ቢቋቋም የተሻለ ነው የሚል አመለካከት አለኝ።ደራሲ ታክሎ ተሾመ፤ የቀድሞው በታዝማኒያ የኢትዮጵያውያን ማኅበረሰብ ማኅበር ፕሬዚደንት