ከሳሪስ እስከ ሜልበር፤ “አገር - አገር ናት ቢኖራትም ባይኖራትም” ጋዜጠኛ ኤልያስ ጉዲሳ

Elias Gudisa

Elias Gudisa Source: Elias

ጋዜጠኛ ኤልያስ ጉዲሳ፤ ስለ ውልደትና ዕድገቱ፣ የትምህርትና የሥራ ዓለም ጉዞው፣ የስደት ሕይወት ተግዳሮቶችና መልካም ዕድሎች፣ የወደፊት ተስፋና ሕልሞቹን አሰናስሎ ያወጋል።


ውልደትና ዕድገት

የወላጆቹ የበኩር ልጅ የሆነው ጋዜጠኛ ኤልያስ ጉዲሳ ውልደትና ዕድገት ሳሪስ - አዲስ አበባ ነው።

የአንደኛና መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ቀለም የቀሰመው ሰኔ ዘጠኝ ትምህርት ቤት ሲሆን፤ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ያጠናቀቀው ነፋስ ስልክ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ነው። በዚያም አላበቃም። የሁለተኛ ደረጃ መልቀቂያ ፈተና ውጤቱ መልካም በመሆኑ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲም ዘልቋል።

የሥራ ዓለም - የጋዜጠኝነት ሕይወት ጅማሮ

ኤልያስ - የጋዜጠኝነት ሕይወት ፈልግን መከተል የጀመረው የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ሳለ ነበር። ትምህርት ቤቱን በመወከል ከአቻ ትምህርት ቤት ተማሪዎች ጋር ተወዳዳሪ ሆኖ የጥረቱን ፍሬዎች አይቶበታል። ተሸላሚ ለመሆን በቅቶበታል።

አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሳለም የሬዲዮ ድራማዎችን በመፃፍ የሥነ ጽሑፍ በረከቶቹን እነሆኝ ማለት ጀመረ። የቀለም ትሩፋቶቹ ዩኒቨርሲቲ ቅጥር ግቢ ተወስነውም አልቀሩም። እ.ኢ.አ. በ1989 ዓ.ም በወቅቱ ተወዳጅ የነበረው “የቅዳሜ መዝናኛ ዝግጅት” ስቱዲዮ ደረሰ።

በማኅበራዊና የፍቅር ሕይወቶች ዙሪያ የሚያጠነጥነው የራዲዮ ድራማው የአየር ሞገድ አሳብረው አደባባይ ዋሉ። ከአድማጮች ጆሮ ዘለቁ። ለሶስት ሳምንታት በተከታታይ በኢትዮጵያ ራዲዮ ሞገድ ላይ ናኙ።

የቀለም ጠብታው ጭማቂዎቹ ከራዲዮ ጣቢያው የመጀመሪያውን የሥራ ዋጋ ክፍያ፤ ከአድማጮች አበረታች ግብረ ምላሾችን አስገኘለት። ከወቅቱ የመጽሔት አሳታሚዎች ጋርም ለትውውቅ አበቁት።  

የሕይወት ጥሪውን ተከትሎ ለሶስት ወራት በተከታታይ ለጋዜጦችና መጽሔቶች ጽሑፎችን ማቅረብ ጀመረ። ከሩብ ዓመት በኋላ ራሱን ችሎ የሕትመት ውጤቶችን ለአንባቢያን ለማድረስ ተነሳሳ።

የመጀመሪያ የሕትመት ውጤቱ የሆነችው “ቃል ኪዳን” ጋዜጣ አሳታሚ ሆነ። የጋዜጣይቱ ተነባቢነት እየጨመረ መጣ። ቃል ኪዳን - በሳምንት አንዴ ከመውጣት በሳምንት ሁለቴ አንባቢያን እጅ መግባት ጀመረች።

ሲልም፤ እ.ኢ.አ. በ1990 የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ሲከፈት ፓለቲካ ተኮር የሆነችውን “ትኩሳት” ጋዜጣ አከለ። ትኩሳት - በገቢም በተደራሽነትም ስኬታማ ለመሆን በቃች። ከሁለት ዓመታት በኋላ “ረመጥ” ጋዜጣን ሶስተኛ የሕትመት ውጤቱ አድርጎ ማሳተም ያዘ።
Tikusat
Source: Elias Gudisa
ኤልያስ - በዚህም አላበቃም። እ.ኢ.አ. በ1994 “ቃል ኪዳን” ጋዜጣ ላይ “ቃል ኪዳን” መጽሔትን ጨመረ። የጋዜጦቹና መጽሔቱ ሕትመት ውጤቶችም ለበርካታ ጋዜጠኞች የሥራ ዕድሎችንም ከፍቷል።

ሆኖም ጥቂት ቆይቶ በኢትዮጵያ መንግሥት በኩል አሳታሚዎች በአንድ የሕትመት ዘርፍ ብቻ መርጠው እንዲሠሩ የሚል አስገዳጅ ድንጋጌ በማውጣቱ ጋዜጦቹን ዘግቶ በ”ቃል ኪዳን” መጽሔት ሕትመት ብቻ ተወሰነ።

ቀደም ሲል በማኅበራዊ ሕይወት ላይ ብቻ ታተኩር የነበረችው ቃልኪዳን በጥምረት ፖለቲካዊ ጉዳዮችንም አካትታ ይዛ መውጣት ጀመረች። ፖለቲካዊ ትኩረቷ ግና መዘዞችን አስከተሉ።

ኤልያስን ወደ አገረ ኬንያ ለስደት ዳረጉ።

ከ2 ዓመታት ከ11 ወራት በኋላም ለአገረ አውስትራሊያ አበቁ።

ኑሮ በአውስትራሊያ

ኤልያስ - የአውስትራሊያን ቀይ አፈር ለመጀመሪያ ጊዜ የረገጠው የምዕራብ አውስትራሊያ ክፍለ አገር ዋና ከተማ ፐርዝ ሲሰፍር ነው። እምብዛም ሳይቆይ ግና በአራተኛ ወሩ የቪክቶሪያ ክፍለ አገር ዋና ከተማ ወደ ሆነችው ሜልበርን አቀና።  
Elias Gudisa
Elias Gudisa Source: Elias
ሜልበር ከአውስትራሊያ ክፍለ አገራት ሁሉ የበርካታ ኢትዮጵያውያን መኖሪያ በመሆኗ የጋዜጠኝነት ሕልሙን ዕውን ለማድረግ አለመ።

የ “ቃል ኪዳን” መጽሔትን በአገረ አውስትራሊያ “ሀ” ብሎ ጀመረ። ይዞ የተነሳው ዓላማ ለገቢ ማስገኛነት ሳይሆን የሙያ ፍቅርን በመወጣት ለራስ ማኅበረሰብ ግልጋሎትን ለማበርከት ነው።
Promise
Source: Elias Gudisa
እስካሁን አራት የቃል ኪዳንን ዕትሞችን ለአንባቢያን አቅርቧል።         

ኑሮን ለማሸነፍ ለአንድ የምግብ ምርት ኢንዱስትሪ ግልጋሎት ሰጪ ኩባንያ Site Manager ሆኖ እየሠራ ይገኛል።

ለSBS አማርኛ ክፍል በሪፖርተርነት ሙያዊ አስተዋጽኦ እያበረከተ አለ።

 

 

 


Share
Follow SBS Amharic

Download our apps
SBS Audio
SBS On Demand

Listen to our podcasts
Independent news and stories connecting you to life in Australia and Amharic-speaking Australians.
Ease into the English language and Australian culture. We make learning English convenient, fun and practical.
Get the latest with our exclusive in-language podcasts on your favourite podcast apps.

Watch on SBS
SBS World News

SBS World News

Take a global view with Australia's most comprehensive world news service
ከሳሪስ እስከ ሜልበር፤ “አገር - አገር ናት ቢኖራትም ባይኖራትም” ጋዜጠኛ ኤልያስ ጉዲሳ | SBS Amharic