ቤተሰብ ምስረታ
አቶ ታክሎ የሱዳንን ድንበር ተሻግረው ለስደተኝነት የተዳረጉት ድርጅታቸው ኢሕአፓ የደርግ አገዛዝ ዒላማ በመሆኑ ልባቸው ተገዢ የነበረው ለኢሕአፓ ፍቅር እንጂ ለተቃራኒ ፆታ አልነበረም።
ታላቁ መፅሐፍ "ለሁሉም ጊዜ አለው" እንዲል፤ፍቅራቸውን ለዛሬዋ ባለቤታቸው ወ/ሮ ገበያነሽ አጋሩ።
ቀለበት ተሳሰሩ።

አዲሶቹ ባለ ቀለበቶች ወራት አስቆጥረው የመጀመሪያ ልጃቸውን አፈሩ።
ስሟን "አበባ" ሲሉ ሰየሙ።
ጉዞ ወደ አውስትራሊያ
አውስትራሊያ አቶ ታክሎን፣ ባለቤታቸውን ወ/ሮ ገበያነሽንና ልጃቸውን አበባን ተቀበለች።
አዲሱ መኖሪያቸውም በጣት የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ይኖሩባት የነበረችው ሆባርት - ታዝማኒያ ሆነ።

እምብዛም ሳይቆዩ ግና እስካሁንም ወደ አሉባትና በርካታ ኢዮጵያውያን ወደ ሚኖሩባት ሜልበርን ከተማ ጓዛቸውን ሸክፈው ከቤተሰባቸው ጋር ከተሙ።
በዓመታት ቆይታቸው ቤተሰባቸው በልጆች በረከት ተመላ። ቁጥሩም በረከተ።

ደራሲ ታክሎ ተሾመ፤ በግል ኑሯቸው ደስተኛ እንደሆኑ ይገልጣሉ።
'የኢትዮጵያውያን ማኅበረሰብ አባላት ማኅበራዊ አኗኗርና አገራዊ ተሳትፎ ጥንካሬው የላላ ነው' የሚል አተያይም አላቸው።







