ውልደትና ዕድገት
ወ/ት ናዲያ - ከአባታቸው ፔይትሮ ሞናያ እና ከእናታቸው ግላዲስ ይማም አብራክ የተከፈሉት አዲስ አበባ ከተማ ነው።

የበኩር ልጅ ናቸው። ተከታይ እህትና ወንድም አላቸው።
የዘመናዊ ሁለተኛ ደረጃ ቀለም ትምህርታቸውን እ.አ.አ በ1997 ያጠናቀቁት በሊሴ ገብረማርያም ትምህርት ቤት ነው።

በእዚያም አላበቁ፤ የከፍተኛ ተቋም ትምህርታቸውን ለመቀጠል ባሕር ማዶ ተሻገሩ።
የዩኒቨርሲቲ ትምህርት ቀሰማ
ወ/ት ናዲያ ከሀገር ቤት ወደ ባሕር ማዶ ቀድመው ያቀኑት አንደኛው የማንነታቸው ጎን መፍለቂያ ወደ ሆነችው ሀገረ ጣልያን ነው።
የጣሊያኑ University of Trieste በሩን ከፍቶ ተቀበላቸው።
በመማሪያ ክፍሎቹም ዓለም አቀፍ እና የዲፕሎማሲ ሳይንስ አጠኑበት።
የሶስተኛ ዓመት ተማሪ ሳሉ የ Erasmus የፖለቲካ ሳይንስ ቋንቋዎች ፕሮግራም ነፃ ትምህርት ዕድል አሸናፊ ሆኑ።
ወደ ፈረንሳይ መዲና ፓሪስ አመሩ።
ዓረብኛ እና ማንዳሪን ቋንቋዎችን Institut National des Langues et Civilisations Orientales (INALCO) ዘልቀው በ2002 ከወኑ።
ለሶስተኛ ጊዜ ሀገር ቀየሩ። ሳዑዲ ዓረቢያ ገቡ።
በ2025 የእስልምናና ዓረብኛ ቋንቋ ጥናታቸውን መካ ከሚገኘው University of Umm Al-Qura በማዕረግ ተሸላሚ ሆነው ዲፕሎማቸውን ተቀበሉ።
ፊታቸውን ወደ አራተኛዋ ሀገረ አሜሪካ አዞሩ።
College of Southern Nevada ገቡ። በ2013 Associate of Arts (AA) in International Languages አጠናቅቀው የምሩቃን ተማሪዎች ተናጋሪ ጭምር ሆነው ተመረቁ።
ለጥቀውም ወደ አምስተኛዋ የትምህርት ቀሰማ መዳረሻቸው ሀገረ እንግሊዝ ውቅያኖስ አቋርጠው ደረሱ። የመጀመሪያ ሁለተኛ ዲግሪያቸውን በሥርዓተ ትምህርት ከ University of Derby እንዲሁም፤ ተጨማሪ የድኅረ ምረቃ ዲግሪያቸውን በፍልስፍና ከ University of Exeter በ2020 እና 2022 በቅደም ተከተል ተቀበሉ።

በአሁኑ ወቅትም በሥርዓተ ትምህርት ላይ ያተኮረ የሶስተኛ ዲግሪ (PhD) ምርምር ጥናታቸውን ከሳዑዲ ዓረቢያ ሴቶችና መድብለ ባሕል ጋር አሰናስለው በማካሔድ ላይ ይገኛሉ።
የምረቃ ውጥናቸውን በ2027 አድርገው።
ከትምህርትና የአፍ መፍቻ ቋንቋዎቻቸው ጋር ተጣምረውም ሰባት ቋንቋዎችን ይናገራሉ።
ሀገር ቤት ሳሉ በእናት፣ በሴት አያትና አባታቸው አማካይነት አማርኛ፣ ትግሪኛና ጣሊያንኛ የአፍ መፍቻ ቋንቋዎቻቸው ነበሩ።
ፈረንሳይኛ፣ እንግሊዝኛና ማንዳሪን ቋንቋዎችን በትምህርት ቤት ሲካኑ፤ ዓረብኛን በትምህርት ቤትና በኑሮም ጭምር አርቅቀው ይናገራሉ።
ስንኝ ቋጣሪም ስለሆኑ፤ ግጥሞቻቸውን በእንግሊዝኛ፣ አማርኛና ዓረብኛ አራቅቀው ይፅፋሉ።
በሥራ ዓለምም ሳዑዲ ዓረቢያ ውስጥ በዩኒቨርሲቲ ደረጃ የእንግሊዝኛ ቋንቋ መምህርነት ሆነው ሠርተዋል።
በዲፕሎማሲው ዘርፍም በዓለም አቀፍ ግንኙነት መኮንነትና አስተባባሪነት በኦስሎ የሰላም ንግግር ላይ ተሳትፈዋል።
የትምህርትና የሥራ አገልግሎቶቻቸው በባሕር ማዶ ብቻ እንዲወሰኑ አይሹም።
ትምህርትን ማዕከሉ ያደረገውን የሶስተኛ ዲግሪ (PhD) የምርምር ጥናታቸውን ሲያጠናቅቁም ወደ ሀገረ ኢትዮጵያ ዘልቀው ትምህርት ተኮር ፕሮጄክቶችን ለመተግበር ዕሳቤውን ከወዲሁ ለንድፍ አብቅተዋል።
የትልቅ ግብር መነሻ ከብሩህ አዕምሮ የሚፈልቅ ትልም ነውና።
ሙያዬ በትምህርቱ ዘርፍ ስለሆነ 'እንደምን አድርገን ነው የትምህርት ተደራሽነት እንዲስፋፋ የምናደርገው? ሥርዓተ ትምህርቱንና የትምህርት ጥራትን የምናሻሽለው? በሚሉና ሴቶቻችንን በምንደግፍባቸው የተለያዩ ፕሮጄክቶች ውስጥ አስተዋፅዖ ማድረግን እሻለሁ።ናዲያ ሞናያ - የሶስተኛ ዲግሪ (PhD) ተማሪ






