አቶ አበበ በለጋ ሕይወታቸው የ1966ቱን የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮት ንቅናቄ ተከትሎ በወቅቱ ስመ ገነን የነበረው የኢትዮጵያ ሕዝብ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) ወጣቶች ክንፍ የሆነው የኢትዮጵያ ሕዝብ አብዮታዊ ወጣቶች ሊግ (ኢሕአወሊ) አባል ሆኑ።

እንደ ዘመናቸው ወጣቶች ኢትዮጵያን በሶሻሊስታዊ ሥርዓት ለመታደግ።
ሆኖም፤ የመጨረሻው የኢትዮጵያ ዘውዳዊ የአገዛዝ ሥርዓት ሲያከትም ሥልጣነ መንግሥቱ በወቅቱ አዲስ በተመሠረቱት የፖለቲካ ድርጅቶች እጅ ሳይሆን በአገሪቱ የጦር ኃይሎች መዳፍ ስር ወደቀ።
የወጣቱ አበበ ጽጌ ፓርቲ - ኢሕአፓም ዋነኛ የፖለቲካ ስልጣን ተቀናቃኝ ሆኖ ቀረበ። “ያለ ምንም ደም - ኢትዮጵያ ትቅደም” የተዘመረለት አብዮት አያሌ ወጣቶችን ለእሥራት፣ ስደትና ሕልፈተ ሕይወት ዳረገ።
የወጣቱ አበበ ዕጣ ፈንታም እሥራትና ስደት ሆነ።
የሱዳን አጎራባቿ ጎንደር፤ ለአቶ አበበ የኢትዮጵያን ድንበር በእግር መሻገሪያ ሆነች። የሱዳን ምድርም ወጣቱ አበበን ከባላገርነት ወደ ስደተኛነት ለወጠች።
ለስደት ያበቃቸው ፖለቲካዊ አተያይና የኢሕአፓ አባልነታቸው ሱዳንም አልለያቸው አለ።
ይሁን’ጂ ከሱዳን አውጥቶ ለኒውዚላንድ፣ ሲልም፤ ለአገረ አውስትራሊያ ነዋሪነትና ቤተሰብ ምሥረታ አብቅቷቸዋል።

አገሩን ለሚያፈቅር ሰው ባሕር ማዶኛነት አገሩን ከውስጡ አስወጥቶ አያስረሳምና፤ አቶ አበበ ዛሬም - ከአድማስ ባሻገር ስለ አገራቸው መልካሙን ያልማሉ።
ኢትዮጵያዊነት በምድረ ኢትዮጵያ እንዲያብብ።
የለጋ ወጣት ሕይወት ምኞታቸውም በአገረ ኢትዮጵያ ዕውን ሆኖ ለማየት ተስፋ ያደርጋሉ።
ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ቆሞ፤ ፍትሓዊ እኩልነት ሰፍኖ።
እስከዚያው ድረስ ግና ባሉበት አገረ አውስትራሊያ ለኢትዮጵያውያን ማኅበረሰብ የበኩላቸውን አስተዋጽዖዎች በመቸሩ ይገፋሉ።





