አዳሙ ተፈራ - ከደብረ ዘይት እስከ ሜልበርን - አውስትራሊያ

My Story Adamu Tefera

Adamu Tefera Source: Supplied

አቶ አዳሙ ተፈራ የሜልበርን ከተማ ነዋሪ ናቸው። ከልደት እስከ ዕድገት፤ ከሶቪየት ኅብረት እስከ የአውስትራሊያ ዜግነት ያለ ግለ ታሪካቸውን ነቅሰው ያወጋሉ።


ውልደትና ዕድገት

የትውልድ ከተማቸው ደብረ ዘይት ብትሆንም፤ ገና የአራት ዓመት ሕጻን ሳሉ ነበር ለአዲስ አበባ ኑሮ ጉዟቸውን ከወላጆቻቸው ጋር ያቀኑት።

ወላጆቻቸው እሳቸውን ብቻ አላፈሩም። ከአምስት እህቶችና አንድ ወንድም ጋር በደም አቆራኝተዋቸዋል።

የአዲስ አበባ ኑሯቸውንም በቦሌ ክፍለ ከተማ ቆርቁረዋል።  

ወጣቱ አዳሙ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ያጠናቀቀው የአዲስ አበባን ውኃ ጠጥቶ ነው። ቀጣዩን የከፍተኛ ተቋም ትምህርቱን በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለመቀጠል ቢመዘገብም የሕይወት ዕጣ ፈንታው የመራው ወደ ቀድሞይቱ ሶቪየት ኅብረት ነው። በነፃ የትምህርት ዕድል።
My Story Adamu Tefera
ጉዞ ወደ ሶቪየት ኅብረት Source: Supplied
ከሶቭየት ኅብረት ወደ ደቡብ ኢትዮጵያ

አቶ አዳሙ በአገረ ሶቭየት ኅብረት የብሔራዊ ፕላን ምጣኔ ሃብት ትምህርታቸውን በሁለተኛ ዲግሪ ምረቃ እንዳጠናቀቁ ምልሰታቸው ያደረጉት ወደ አገር ቤት ነው።
My Story Adamu Tefera
ሶቪየት ኅብረት Source: Supplied
አገር ቤት እንደተመለሱም በደቡብ ኢትዮጵያ የቀጣና ፕላን ጽሕፈት ቤት ረዳት የትራንስፖርትና መገናኛ ኤክስፐርት ሆነው ተመደቡ።

እምብዛም ሳይቆዩ በዓመቱ የሲዳማ ክፍለ አገር የኢትዮጵያ ሠርቶ አደሮች ቁጥጥር ኮሚቴ ኮሚቴ ሶስተኛ የሥራ አስፈጻሚ አባል ሆኑ።

ስደትና ባሕር ማዶኛነት

እ.አ.አ በ1947 በምሥራቁ የሶሻሊስት ጎራና በምዕራቡ የካፒታሊስት ካምፕ የተጀመረው ቀዝቃዛው ጦርነት በካፒታሊስቱ ካምፕ በ1991 ድል ነሺነት ሲያከትም ለ17 ዓመታት ከሶሻሊስቱ ጎራ ወግኖ የነበረው የኢትዮጵያ ሕዝባዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢሕዲሪ) መንግሥት ዘመንም በኃይል ተገርስሶ አበቃ።

ኢሕዲሪ ሰልፉን ባስተካከለው የኢሕአዴግ ጊዜያዊ መንግሥት አገዛዝ ተተካ። እንደ አያሌ በ10 ሺህዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ሁሉ አቶ አዳሙም ለስደት በቁ። የኬንያን ድንበር ተሻግረው ጥገኝነት ጠየቁ። ከጥቂት ወራት የኬንያ ስደት በኋላም በአውስትራሊያ ሰብዓዊ የስደተኞች ቅበላ ፕሮግራም ሳቢያ የአውስትራሊያ ነዋሪ ለመሆን ቻሉ።

የኑሮ ጅማሮ በአገረ አውስትራሊያ

የአገረ አውስትራሊያ ሥርዓተ መንግሥት አቶ አዳሙ ቀደም ሲል ከነበሩባቸው የሶቪየት ኅብረትም ሆነ የኢትዮጵያ ሶሻሊስታዊ ሥርዓታት የተለየ በመሆኑ ቅኝታቸውን ለማስተካከል ፊታቸውን ወደ ዩኒቨርሲቲ መለሱ። በቢዝነስ ምጣኔ ሃብት ትምህርት በሁለተኛ ዲግሪም ተመረቁ።
My Story Adamu Tefera
ምረቃ በአውስትራሊያ ዩኒቨርሲቲ Source: Supplied
የኑሯቸውን የወደፊት አቅጣጫ በመልካም ጎኑ ቢቀይሱም የኬንያን ድንበር የተሻገሩትና አውስትራሊያንንም ሁለተኛ አገራቸው ያደረጉት ከባለቤታቸው ጋር አልነበረም። ያም በምናባዊ ምልሰት ወደ ቤተሰባቸው ካድማስ ባሻገር እንዲመላለሱ አድርጓቸዋል።

የማኅበረሰብ አገልግሎት

አቶ አዳሙ ማለፊያ ከሚሏቸውና ከወላጆቻቸው ከወረሷቸው ዕሴቶች ውስጥ አንዱ ማኅበራዊና ሕዝባዊ ግልጋሎቶችን መስጠት በመሆኑ ለሶስት ጊዜያት በተደጋጋሚ የቪክቶሪያ የኢትዮጵያውያን ማኅበረሰብ ማኅበር ፕሬዚደንት ሆነው በመመረጥ ሁኔታዎች የፈቀዷቸውን ግልጋሎቶች አበርክተዋል።

ኢትዮጵያና አውስትራሊያ

አቶ አዳሙ “ኢትዮጵያና አውስትራሊያ ለእኔ አንድም የተለያዩም ናቸው” ቢሉም፤ ይላሉ። የአውስትራሊያ ኑሯቸውን የሚያዩት ከእሳቸው ዐልፎ ሁለት ልጆቻቸው ለባለ ሙያነት እንዲበቁ በረከቷን የቸረቻቸው መልካም አገር አድርገው ነው።
ኢትዮጵያና አውስትራሊያ ለእኔ አንድም የተለያዩም ናቸው
ለኢትዮጵያም በቀሪ ሕይወታቸው በተለያዩ ዘርፎች ግልጋሎታቸውን መለገስ ከወደፊት ውጥኖቻቸው ግንባር ቀደሙ ነው።


Share
Follow SBS Amharic

Download our apps
SBS Audio
SBS On Demand

Listen to our podcasts
Independent news and stories connecting you to life in Australia and Amharic-speaking Australians.
Ease into the English language and Australian culture. We make learning English convenient, fun and practical.
Get the latest with our exclusive in-language podcasts on your favourite podcast apps.

Watch on SBS
SBS World News

SBS World News

Take a global view with Australia's most comprehensive world news service