የኔ ታሪክ፤ ጋዜጠኛ ማርታ ፀጋው - ከኮልፌ ወደ አውስትራሊያ

My Story: Martha Tsegaw

Journalist Martha Tsegaw Source: SBS Amharic

ጋዜጠኛ ማርታ ፀጋው ምንዳ - ትውልድና ዕድገቷ ኮልፌ - አዲስ አበባ ነው።በጢያራ የአፍሪካን አየር ሰንጥቃ ከአገረ ኢትዮጵያ ወደ አውስትራሊያ ከዘለቀች ከአንድ አሠርት ዓመት በላይ አስቆጥራለች።


ወላጆች

የማርታ እናት ወይዘሮ አስረሱ በቀለ ይባላሉ። በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል በሕክምና ሙያ የተሰማሩ ነበሩ። ዛሬም ድረስ በሕይወት አሉ። በጊዜያዊነት እየኖሩ ያሉትም እዚሁ አውስትራሊያ ከልጃቸውና የልጅ ልጆቻቸው ጋር ነው።
My Story: Martha Tsegaw
Martha Tsegaw (L), Asresu Bekele (R) Source: Courtesy of MT
አባቷ ፀጋው ምንዳ - በውትድርናው ዘርፍ እስከ ሻምበል ማዕረግ ደርሰዋል። የውትድርና ተግባራቸውን ለመፈጸም ኤርትራ ዘምተው ሳለ መተኪያ የሌላት ውድ ሕይወታቸውን መተኪያ ለሌላት ውድ አገራቸው ኢትዮጵያ ለወቅቱ የአንድነት ትግል ያለ ስስት ሰውተዋል።
My Story: Martha Tsegaw
Captain Tsegaw Menda (L), and Asresu Bekele (R) Source: Courtesy of MT
የትምህርት ዓለም

የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቷን የተከታተለችው በኮልፌ የሰላም በር አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ሲሆን፤ እስከ 12ኛ ደረጃ ያለውን ትምህርቷን ያጠናቀቀችው በኮልፌ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ነው።

 በእናቷ የሕክምና መስክ መሰማራት ሳቢያ የልጅነት የቀለም ሕይወቷ ተጠቅሶ የነበረው ነርስ ወይም ሐኪም እንድትሆን ነበር። ያም ወደ ሳይንስ ትምህርት እንድታመዝን አድርጓታል። ይሁን’ጂ ወደ ዩኒቨርሲቲ ስትዘልቅ የገጠማት የጥናት መስክ የቋንቋና ሥነ ጽሑፍ ዘርፍ ነው።

 ከትምህርት ቤት ወደ ጋዜጠኛነት

ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የዲፕሎማ ምሩቅነት በኋላ የሙያ ጅምሯ በኢትዮጵያ ራዲዮ ነበር። ሲልም፤ FM Addis 97.1 ሌላኛው የኢትዮጵያ ራዲዮ ልሳን ሆኖ ሲቋቋም ከመሥራቾቹ አንዷ ሆና ወደዚያ በመዞር ለሁለት ዓመታት አገልግላለች። በጥቅሉ ወደ አውስትራሊያ እስክታመራ ለአራት ዓመታት በራዲዮ ጋዜጠኛነት ሠርታለች።
My Story: Martha Tsegaw
Martha Tsegaw FM 97.1 Source: Courtesy of MT
ከኮልፌ ወደ አውስትራሊያ

የማርታ ወደ አገረ አውስትራሊያ አመጣጥ በጋብቻ ነው።
My Story: Martha Tsegaw
Martha's husband Woldemichael Addis and Martha Tsegaw Source: Courtesy of MT
እንደማንኛውም አዲስ ሠፋሪ ከአዲሲቷ የመኖሪያ አገሯ አውስትራሊያ ጋር መላመድ፣ ራስን ከአገሬው የአኗኗር ዘይቤ ጋር ማዋደድ፣ የወጣትነት ሕልሞችን ዕውን ለማድረግ በእጅጉ ጉጉ የመሆን የሕይወት ጉዞ ውስጥ ከነተግዳሮቱና ስኬቱ አልፋለች።
My Story: Martha Tsegaw
Martha Tsegaw (1995 L), and (2017 R) Source: Courtesy of MT
የአገር ቤት የራዲዮ ጋዜጠኛነት መንፈሷ ሳይበርድ፤ የአውስትራሊያ የመጀመሪያ ሥራዋ የሆነው የልብስ ድርደራ - ፈታኝ የባሕር ማዶ ሕይወት ሽግግር ዕውነታ ሆኖ ውስጧን ፈትኖታል።

 ከሁለት ዓመታት የባሕር ማዶ ሕይወት ወጀብ መዋለል በኋላም ቋሚ የመኖሪያ ፈቃዷን አገኘች። የመጀመሪያ ወንድ ልጇንም አቅፋ ሳመች። ገና ከአራስ ቤት ሳትወጣ ዳግም ራሷን በትምህርት የመለወጡ የተዳፈነ የጉጉት ፍም ነድዶ ወጣ። የመጀመሪያ ልጇን በወለደች ሶስተኛ ወሯ የዩኒቨርሲቲ በር አንኳኳች። ተቀባይነት አግኝታም ከRMIT በአስተርጓሚና ተርጓሚነት በዲፕሎማ ተመረቀች። እምባዛም ሳትቆይ በ Community Development ከቪክቶሪያ ዩኒቨርሲቲ የመጀመሪያ ዲግሪዋን ተቀበለች።
My Story: Martha Tsegaw
Martha Tsegaw Source: Courtesy of MT
በአውስትራሊያ ቆይታዋ ከትዳር ሕይወቷ የ14 - የ13 እና ስምንት ዓመት ዕድሜ ያላቸው ሶስት ወንዶች ልጆች እናት ሆናለች። የወደፊት ተስፋና ምኞቶቿ ከሚያርፉባቸው የሕይወት ንድፎቿ ቀዳሚዎቹ ልጆቿ መሆናቸውም እውነት ነው።
My Story: Martha Tsegaw
Mabi, Yosef, Martha, and Bereket Source: Courtesy of MT
ተስፋና ምኞት

የማርታ ፀጋው - የወደፊት ተስፋና ምኞቶች የተቃኙት በቤተሰብና በአገር ሶስት ዋነኛ ትልሞቿ ዙሪያ ነው።

የመጀመሪያው - ልጆቿ በዕውቀት ጎልምሰው፣ ማለፊያ ሥራ ይዘው፣ ውጤታማ ዜጎች ሆነው ማየት፤

ሁለተኛው - በተሰማራችበት የሥራ ዓለም ውስጥ ተወዳዳሪ ሆና መዝለቅ ሲሆን፤

ሶስተኛው - ኢትዮጵያ ትልቅ የዕድገት ደረጃ ላይ ደርሳ ማየትና ለዕድገቷም በተቻለ መጠን በአንድ ዘርፍ አስተዋፅዖ ለማበርከት እችላለሁ የሚል ነው።

ማርታ ፀጋው - በአውስትራሊያ የ SBS አማርኛ ገዲብ ሪፖርተር ሆና እያገለገለች ትገኛለች። ለላቀው ሙያዊ አስተዋፅዖዎቿም አድናቆታችን ከፍ ያለ ነው።

 

 


Share
Follow SBS Amharic

Download our apps
SBS Audio
SBS On Demand

Listen to our podcasts
Independent news and stories connecting you to life in Australia and Amharic-speaking Australians.
Ease into the English language and Australian culture. We make learning English convenient, fun and practical.
Get the latest with our exclusive in-language podcasts on your favourite podcast apps.

Watch on SBS
SBS World News

SBS World News

Take a global view with Australia's most comprehensive world news service
የኔ ታሪክ፤ ጋዜጠኛ ማርታ ፀጋው - ከኮልፌ ወደ አውስትራሊያ | SBS Amharic